“ታህሳስ 26–ጥር 1 (እ.አ.አ)። እኛ ለራሳችን መማር ሀላፊነት አለብን፣” ኑ፣ ተከተሉኝ—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች፦ አዲስ ኪዳን 2023 (እ.አ.አ) [2022 ( እ.አ.አ)]
“ታህሳስ 26–ጥር 1 (እ.አ.አ)። እኛ ለራሳችን መማር ሀላፊነት አለብን፣” ኑ፣ ተከተሉኝ—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች፦ 2023 (እ.አ.አ)
ታህሳስ 26–ጥር 1 (እ.አ.አ)
እኛ ለራሳችን መማር ሀላፊነት አለብን
የቅዱሳት መጻህፍት ዋና አላማ ወደ ክርስቶስ እንድትመጡ እና ይበልጥ በጥልቀት ወደ እሱ ወንጌል እንድትቀየሩ መርዳት ነው። ኑ፣ ተከተሉኝ—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች ቅዱሳት መጻህፍትን እንድትረዱ እና እናንተ እና ቤተሰቦቻችሁ የሚያስፈልጋችሁን መንፈሳዊ ጥንካሬ እንድታገኙባቸው ሊረዳችሁ ይችላል። ከዚያም በቤተክርስትያን ክፍሎቻችሁ መረዳታችሁን የማካፈል እናም ቅዱሳን ጓደኞቻችሁ ክርስቶስን ለመከተል በሚያደርጉት ጥረቶች ብርታትን ለመስጠት እድል ይኖራችኋል።
ያሳደረብዎትን ስሜት ይመዝግቡ
“ምን ትፈልጋላችሁ?” ኢየሱስ የመጥምቁ ዮሐንስን ደቀመዛሙርት ጠየቀ (ዮሐንስ 1፥38)። እናንተም ተመሳሳይ ጥያቄ ራሳችሁን ልትጠይቁ ትችላላችሁ—ምክንያቱም በዚህ አመት በአዲስ ኪዳን የምታገኙት በምትፈልጉት ነገር ላይ በእጅጉ ይወስናልና። “ፈልጉ ታገኙማላችሁ፣” የአዳኙ ቃል ኪዳን ነው (ማቴዎስ 7፥7)። ስለዚህ ስታጠኑ ወደ አዕምሯችሁ የሚመጡ ጥያቄዎችን ጠይቁ፣ ከዚያም መልሶችን በትጋት ፈልጉ። በአዲስ ኪዳን ውስጥ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዛሙርት በሃይል የተሞላ መንፈሳዊ ልምምዶች ታነባላችሁ። እንደ ታማኝ የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዛሙርት፣ በዚህ በ“ኑ፣ ተከተሉኝ” (ሉቃስ 18፥22) የተቀደሰ ቅጂ ሙሉ የሚገኘውን የአዳኙን ግብዣ ስትቀበሉ፣ የራሳችሁ በሃይል የተሞላ መንፈሳዊ ልምምዶች ሊኖራችሁ ትችላላችሁ።
ለግል የቅዱሳት መጻህፍት ጥናት ሃሳቦች
ከአዳኙ በእውነት ለመማር የእርሱን “ኑ፣ ተከተሉኝ” ግብዣን መቀበል አለብኝ።
በደቀመዛሙርትነት ጎዳና ላይ አዲስ ብንሆን ወይም በእድሜያችን ሙሉ ተራምደነው ብንሆንም፣ የአዳኙ “ኑ፣ ተከተሉኝ” ግብዣ ለሁሉም የተሰጠ ነው። ትዕዛዛትን ለመጠበቅ ይተጋ ለነበረ አንድ ሃብታም ሰው ይህም ነበር ግብዣው (ማቴዎስ 19፥16–22፤ ሉቃስ 18፥18–23ን ተመልከቱ)። ያ ወጣት የተማረው—እና እኛም መማር ያለብን—ደቀመዛሙርትነት ማለት ሙሉ ነፍሳችንን ለሰማይ አባት እና ለኢየሱስ ክርስቶስ መስጠት ማለት እንደሆነ ነው። የሚጎለንን ስንለይ፣ ለውጥ ስናመጣ እና ይበልጥ እነርሱን በሙላት ለመከተል ስንሻ በደቀመዝሙርነታችን እያደግን እንመጣለን።
ከአዳኙ መማር የሚጀምረው እርሱ ያስተማረንን ለመረዳት ስንጥር ነው። ለምሳሌ የሚከተሉትን ስታጠኑ ስለ ትህትና ያላችሁ መረዳት ጥልቀት እንዴት ይጨምራ?
-
የአዳኙ አስተምሮቶች (ማቴዎስ 18፥1–5፤ ሉቃስ 18፥9–14ን ተመልከቱ)
-
ከእርሱ ህይወት ምሳሌ (ዮሐንስ 13፥1–15ን ተመልከቱ)
የበለጠ መማር ከፈለጋችሁ ይህንን ስራ እንደ ፍቅር ወይም ይቅርታ አይነት ከሆነ ከሌላ የወንጌል መርህ ጋር ተግብሩት።
እኔ ለራሴ መማር ሀላፊነት አለብኝ።
ሽማግሌ ዴቪድ ኤ ቤድናር እንዳስተማሩት፦ “ቤተክርስቲያኗ እንደ ተቋም ድርጅት እኛ መለኮታዊ ደቀመዛሙርት ለመሆን እና እስከመጨረሻ በጥንካሬ ለመፅናት ማወቅ ወይም ማድረግ የሚያስፈልጉንን ሁሉ እንድታስተምረን ወይን እንድትነግረን መጠበቅ አይገባንም። ይልቁንም፣ የግል ሀላፊነታችን መማር ያለብንን መማር፣ መኖር እንዳለብን በምናውቀው መልኩ መኖር፣ እናም መምህሩ እንድንሆን የሚፈልገውን መሆን ነው። ቤታችን ለመማር፣ ለመኖር፣ እና ለመሆን ዋነኛ አመቺ ስፍራ ነው” (“ማንኛውንም አስፈላጊ ነገር ለማግኘት ተዘጋጁ፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2019 (እ.አ.አ)፣ 102)።
ለራሳችሁ መማር ሀላፊነት መውሰድ ምን ማለት ነው? መልስ ሊሆኑ የሚችሉትን በሽማግሌ ቤድናር ንግግር እና በሚከተሉት ጥቅሶች ፈልጉ፦ ዮሐንስ 7፥17፤ 1 ተሰሎንቄ 5፥21፤ ያዕቆብ 1፥5–6፣ 22፤ 2፥17፤ 1 ኔፊ 10፥17–19፤ 2 ኔፊ 4፥15፤ አልማ 32፥27፤ እና ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 18፥18፤ 58፥26–28፤ 88፥118። ወንጌልን በንቃት ለመማር ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ምን መነሳሻ ይሰማችኋል?
እኔ እውነትን ለራሴ ማወቅ አለብኝ።
በህይወታቸው ምንም ቢከሰት ፈጽሞ እምነት የሚያጡ የማይመስሉ ሰዎችን ምናልባት ታውቁ ይሆናል። እነርሱም በአዳኙ ምሳሌ ውስጥ የነበሩ አምስቱን ልባም ቆነጃጅት ሊያስታውሷችሁ ይችላሉ (ማቴዎስ 25፥1–13ን ተመልከቱ)። እናንተ ላታዩት የምትችሉት እነርሱ የእውነት ምስክርነታቸውን ለማጠንከር የሚያደርጉትን ብርቱ ጥረት ነው።
እንዴት ነው የራሳችንን ምስክርነት ልናገኝ እና ልናሳድግ የምንችለው? የሚከተሉትን ጥቅሶች ስታሰላስሉ ሃሳባችሁን መዝግቡ፦ ሉቃስ 11፥9–13፤ ዮሐንስ 5፥39፤ 7፥14–17፤ የሐዋርያት ስራ 17፥10–12፤ 1 ቆሮንቶስ 2፥9–11፤ እና አልማ 5፥ 45–46። (በተጨማሪም ከወንጌል ርዕሶች “ምስክርነት፣” topics.ChurchofJesusChrist.orgን ይመልከቱ።)
እያንዳንዳችን የራሳችን ምስክርነት ማግኘት ይኖርብናል።
ጥያቄዎች ሲኖሩኝ ምን ማድረግ ይገባኛል?
መንፈሳዊ እውቀትን ስትሹ፣ ጥያቄዎች ወደ አዕምሮዓችሁ ይመጣሉ። የሚከተሉት መርሆዎች እምነትን እና ምስክርነትን በሚገነባ መልኩ ጥያቄዎቻችሁን እንድታስተናግዱ ሊረዷችሁ ይችላሉ።
-
መረዳትን ከእግዚአብሔር ፈልጉ። እግዚአብሔር የእውነት ሁሉ ምንጭ ነው፣ እናም በመንፈስ ቅዱስ፣ በቅዱሳት መጻህፍት እና በነቢያቱና ሐዋርያቱ አማካኝነት እውነትን ይገልጣል።
-
በእምነት አድርጉ። መልሶች ወድያው ካልመጡልም፣ ጌታ ጊዜው ትክክለኛ ሲሆን እንደሚገልጥ እመኑ። እስከዚያው ድረስ፣ አስቀድማችሁ በምታውቁት እውነት መኖር ቀጥሉ።
-
ዘለአለማዊ እይታ ይኑራችሁ። ነገሮችን አለም እንደሚያየው ሳይሆን ጌታ እንደሚያየው ለማየት ሞክሩ። ጥያቄዎቻችሁን በሰማይ አባት የደህንነት ዕቅድ አግባብ እዩት።
ለቤተሰብ ቅዱሳት መጻህፍት ጥናትና ለቤተሰብ የቤት ምሽት ሃሳቦች
-
ማቴዎስ 13፥1–23።ቤተሰባችሁ በዚህ አመት ከአዲስ ኪዳን ለመማር እንዲዘጋጅ ለመርዳት፣ የዘሪውን ምሳሌ ማንበብ ትችላላችሁ። ቤተሰባችሁ ወደ ውጭ በመውጣት እና በምሳሌው ላይ ያለውን አይነት የተለያዩ መሬቶችን በመፈለግ ለመደሰት ይችላሉ። ኢየሱስ እንደገለጸው ልባችንን እንደ “መልካም መሬት” ማድረግ የምንችለው እንዴት ነው? (ማቴዎስ 13፥8)።
-
ገላትያ 5፥22–23፤ ፊልጵስዩስ 4፥8።ፕሬዘደንት ራስል ኤም. ኔልሰን እናንተን “ቤታ[ችሁን] ወደ እምነት መቅደስ ቀይሩት” እና “ቤታችሁን እንደ ወንጌል መማሪያ ክፍል ለውጡት” በማለት ጋብዘዋል። እነዚህን ነገሮች ለሚያደርጉም የሚከተለውን ቃል ገብተዋል፦ “ልጆቻችሁ የአዳኙን ትምህርት በመማር እና በመኖር ይደሰታሉ፣ እናም ጠላት በህይወታችሁ እና በቤታችሁ ውስጥ ያለው ተፅዕኖ ይቀንሳል። በቤተሰባችሁ ውስጥ ያለው ለውጥ ታላቅ እና የሚቀጥል ይሆናል” (“ምሳሌያዊ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን መሆን፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2018 (እ.አ.አ)፣ 113)።
ቤታችሁን “ወደ እምነት መቅደስ” እና “የወንጌል መማሪያ ክፍል” ለማድረግ የቤተሰብ ምክክር ለማድረግ የአዲስ አመት መጀመርያ ጥሩ ጊዜ ነው። እኛም ገላትያ 5፥22–23 እና ፍልጵስዩስ 4፥8ን ስናነብ ይህንን ለመፈጸም ወደ አዕምሮ ምን አይነት ሃሳብ ይመጣልናል? ምናልባት በዚህ አመት ቤተሰባችሁ አዲስ ኪዳንን ለማጥናት የግል እና የቤተሰብ ግቦችን ሊያስቀምጥ ይችላል። ራሳችንን ስለ ግባችን ለማስታወስ ምን ማድረግ እንችላለን?
ልጆችን ለማስተማር ተጨማሪ ሃሳቦችን ለማግኘት የዚህን ሳምንት ዝርዝር በ ኑ፣ ተከተሉኝ—ለመጀመሪያ ክፍል ውስጥ ይመልከቱ።
በሀሳብ የሚቀርብ መዝሙር፦ “Teach Me to Walk in the Light [በብርሃን እንድጓዝ አስተምሩኝ]፣” የልጆች መዝሙር መጽሃፍ፣፣ 177።
የግል ጥናትን ማሻሻል
ትምህርቶችን ፈልጉ። ትምህርት ዘላለማዊ፣ የማይለወጥ እውነት ነው። ፕሬዘዳንት ቦይድ ኬ. ፓከር “እውነተኛ ትምህርት ከተረዱት፣ አኳኋንን እና ባህሪይን ይለውጣል” በማለት ገልጸዋል (“ትትንሽ ልጆች፣” ኤንዛይን፣ ህዳር 1986 (እ.አ.አ)፣ 17)። እናንተ እና ቤተሰቦቻችሁ ቅዱሳት መጻህፍትን ስታጠኑ ይበልጥ እንደ አዳኙ ለመኖር የሚያግዟችሁን እውነቶች ፈልጉ።
የአለም ብርሃን፣ በብረንት ቦረፕ