አዲስ ኪዳን 2023 (እ.አ.አ)
መጋቢት 27–ሚያዝያ 2 (እ.አ.አ)። ማቴዎስ 14፤ ማርቆስ 6፤ ዮሃንስ 5–6፦ “አትፍሩ”


“መጋቢት 27–ሚያዝያ 2 (እ.አ.አ)። ማቴዎስ 14፤ ማርቆስ 6፤ ዮሃንስ 5–6፤ ‘አትፍሩ፣’” ኑ፣ ተከተሉኝን—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች፦ አዲስ ኪዳን 2023 (እ.አ.አ) [2022 (እ.አ.አ)]

“መጋቢት 27–ሚያዝያ 2 (እ.አ.አ)። ማቴዎስ 14፤ ማርቆስ 6፤ ዮሃንስ 5–6፣” ኑ፣ ተከተሉኝ—ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች፦ 2023 (እ.አ.አ)

ምስል
ኢየሱስ የዳቦ ቅርጫት ይዞ ከደቀ መዛሙርት ጋር እየተራመደ

መጋቢት 27–ሚያዝያ 2 (እ.አ.አ)

ማቴዎስ 14ማርቆስ 6ዮሐንስ 5–6

“አትፍሩ”

ማቴዎስ 14ማርቆስ 6፤ እና ዮሐንስ 5–6ን ስታነቡ ለእናንተ ትርጉም ያላቸውን እውነቶች ፈልጉ። እነዚህን የመሳሰሉ ጥያቄዎችን ራሳችሁን መጠየቅ ትችላላችሁ፤ “በእነዚህ ምዕራፎች ላይ ያሉ ጽሁፎች ከእኔ ጋር እንዴት ይገናኛሉ?” “ለህይወቴ ምን አይነት መልዕክቶችን አገኛልሁ?” ወይም “ለቤተሰቤ ወይም ለሌሎች ምን ማካፈል እፈልጋለሁ?

ያሳደረብዎትን ስሜት ይመዝግቡ

ጴጥሮስ በገሊላ ሃይቅ፥ ሁከት በበዛበት ማዕበል መሃል መርከቡን ትቶ እንዲሄድ ያነሳሳው ምንድነው? ኢየሱስ ውሃ ላይ መራመድ ከቻለ እሱም እንደሚችል እንዲያምን ያደረገው ምንድነው? በእርግጠኝነት ልናውቅ አንችልም፤ ምናልባት የእግዚአብሔር ልጅ የመጣው ለሰዎች አስደናቂ ነገሮችን ለማድረግ ብቻ ሳይሆን እንደ ጴጥሮስ ያሉ ሰዎችም አስደናቂ ነገር እንዲያደርጉ ለማስቻል ጭምር ሊሆን እንደሚችል ጴጥሮስ ስለተረዳ ሊሆን ይችላል። ያም ሆነ ይህ የኢየሱስ ግብዣ “ኑ፣ ተከተሉኝ” (ሉቃስ 18፥22) ነበር። ጴጥሮስ ይህን ግብዣ አንዴ ተቀብሏል እናም ምንም እንኳን ፍርሃቱን መጋፈጥ እና የማይቻል የሚመስል ነገር ማድረግ ማለት ቢሆንም ዳግም ለመቀበል ዝግጁ ነበር። ምናልባት ጌታ በማዕበል መሃል መርከባችንን ትተን እንድንወጣ ወይም ሺዎች መብላት ሲያስፈልጋቸው በቂ ያልሆነ እንጀራችንን እንድንሰጥ ላይጠይቀን ይችላል፤ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ባልተረዳንበት ሁኔታ ትዕዛዞችን እንድንቀበል ሊጠይቀን ይችላል። ለኛ ግብዣዎቹ ምንም ይሁኑ ምን፣ አንዳንዴ የሚያስገርሙን ወይም ደግሞ የሚያስፈሩን ሊሆኑ ይችላሉ። ነገር ግን እኛ ልክ እንደ ጴጥሮስ ፍርሃታችንን፣ ጥርጣርያችንን እና ውስን መረዳታችንን ወደ ጎን ከተውን ተአምራት ሊከሰቱ ይችላሉ።

ምስል
የግል ጥናት ምልክት

ለግል የቅዱሳት መጻህፍት ጥናት ሃሳቦች

ዮሐንስ 5፥16–47

ኢየሱስ ክርስቶስ አባቱን ያከብራል።

በሰማይ አባት እና በእያንዳንዱ ልጆቹ መካከል ያለው ግንኙነት ቅዱስ እንዲሆን የታሠበ ነው። በእነዚህ ጥቅሶች፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ አባት ጋር ባለን ግንኙነት እንድንከተል የሚያነሳሳ ምሳሌ ሰጥቶናል። ዮሐንስ 5፥16–47ን አንብቡ እናም አባት፣ የሚለውን ቃል ምልክት አድርጉ ወይም ልብ በሉ። ወልድ አባቱን እንዴት ነው ያከበረው እናም የእርሱን ምሳሌ እንዴት መከተል ትችላላችሁ? አብ ስለ ልጁ ስለሚሰማው ነገር ምን ትማራላችሁ? ከሰማይ አባታችሁ ጋር ያላችሁን ግንኙነት ለማጠንከር ምን ማድረግ እንዳለባችሁ ይሰማችኋል?

በተጨማሪም ዮሐንስ 17፤ ጄፍሪ አር. ሆላንድ “የእግዚአብሔር ታላቅነት፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2003 (እ.አ.አ)፣ 70–73 ተመልከቱ።

ምስል
ዳቦ እና አሳ

ኢየሱስ ተአምራዊ በሆነ መንገድ በአምስት እንጀራ እና ሁለት አሳ አምስት ሺህ ሰዎችን መገበ።

ማቴዎስ 14፥15–21ማርቆስ 6፥33–44ዮሐንስን 6፥5–14

አዳኙ የእርሱን ዓላማዎች ለመፈጸም የእኔን ትሁት አቅርቦቶች ከፍ ማድረግ ይችላል።

በዙሪያችሁ የምትመለከቷቸውን ፍላጎቶች በሙሉ—በቤታችሁ፣ በግንኙነቶቻችሁ ወይም በመሃበረሰቡ ውስጥ ለማሟላት ብቁ እንዳልሆናችሁ ሆኖ ተሰምቷችሁ ያውቃል? የኢየሱስ ደቀመዛሙርት አምስት እንጀራ እና ሁለት አሳ ብቻ በነበራቸው ጊዜ ከአምስት ሺህ በላይ የተራቡ ሰዎችን እንዲመግቡ ሲጠይቃቸው በቂ እንዳልሆነ ሆኖ ተሰምቷቸው ይሆናል። ቀጥሎ ስለተፈጠረው ተአምር ስታነቡ፥ የእናንተን አነስተኛ የአገልግሎት አቅርቦት እግዚአብሔር በእናንተ ዙርያ ያሉ ሌሎችን ለመባረክ እንዴት እንደሚጠቀም አሰላስሉ። እርሱን ስታገለግሉት ጥረቶቻችሁን እንዴት ነው ያጎላው? እህት ሚሼል ዲ. ክሬኝ ንግግር ተመልከቱ፤ “እኔ እና እናንተ ያለንን ለክርስቶስ እንሰጣለን እሱም ጥረታችንን ያበዛልናል። ምንም እንኳን በሰው ድካም ቢሆን—በእግዚአብሔር ጸጋ ላይ ተደገፋችሁ እናንተ የምታቀርቡት ከበቂ በላይ ነው” (“መለኮታዊ ቅሬታ፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2018 (እ.አ.አ) 54)።

ማቴዎስ 14፥22–33ማርቆስ 6፥45–52ዮሐንስ 6፥15–21

ኢየሱስ ክርስቶስ ፍርሃቴን እና ጥርጣሬዬን በመተው በእርሱ እምነትን እንድለማመድ ይጋብዘኛል።

ማቴዎስ 14፥22–33ማርቆስ 6፥45–52፤ እና ዮሐንስ 6፥15–21፣ ስለተገለጸው ትዕይንት ዝርዝር በአዕምሯችሁ ሳሉ። ጴጥሮስ እና ሌሎች ደቀመዛሙርት ምን ተሰምቷቸው እንደነበር አስቡ። በእነዚህ ቁጥሮች ላይ ከአዳኙ ቃላት እና ተግባሮች ስለ ደቀ መዝሙርነት ምን ትማራላችሁ? ከጴጥሮስ ቃላት እና ተግባር ምን ትማራላችሁ? (በተጨማሪም 1 ኔፊ 3፥7ን ተመልከቱ።) ጌታ ከመርከብ ላይ እንደመውረድ ሊመስል የሚችል ምን እንድታደርጉ እየጋበዛችሁ ነው? በነዚህ ጥቅሶች ውስጥ በኢየሱስ ክርስቶስ እምነታችሁን እንድትለማመዱ ድፍረት የሚሰጣችሁን ምን ታገኛላችሁ?

ዮሐንስ 6፥22–71

የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር እንደመሆኔ መጠን ማድረግ ከባድ በሚሆንበት ጊዜ እንኳን እውነትን ለማመን እና ለመቀበል ፈቃደኛ መሆን አለብኝ።

ኢየሱስ እራሱን “የሕይወት እንጀራ” ሲል (ዮሐንስ 6፥48)፣ ብዙዎች “የሚያስጨንቅ ንግግር” ሆኖ አገኙት (ዮሐንስ 6፥60)። የአዳኙን ትምህርት መቀበል ወይም መኖር ከባድ በሚሆንበት ጊዜ በዮሐንስ 6፥68–69 ላይ ያለው የጴጥሮስ ቃል እንዴት ይረዳችኋል? ስለ ጴጥሮስ ምስክርነት የሚያስደንቃችሁ ምንድነው? አዳኙን በቁርጠኝነት እንድትከተሉት ከሚረዷችሁ “የዘላለም ሕይወት [ቃላት]” (ዮሐንስ 6፥68) መካከል አንዳንዶቹ የትኞቹ ናቸው?

በተጨማሪም ኤም. ረስል ባላርድ፣ “ወደ ማን እንሄዳለን?፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2016 (እ.አ.አ) 90–92 ን ተመልከቱ።

ምስል
የቤተሰብ ጥናት ምልክት

ለቤተሰብ ቅዱሳት መጻህፍት ጥናትና ለቤተሰብ የቤት ምሽት ሃሳቦች

ማቴዎስ 14፥15–21አምስት ሺህ ሰዎችን ለመመገብ ምን ያህል እንጀራ እና አሳ እንደሚበቃ ቤተሰባችሁ ማሰብ እንዲችል እንዴት መርዳት እንዳለባችሁ አስቡ። በማቴዎስ 14፥15–21 ላይ ያለው ተአምር ስለ አዳኙ ምን ያስተምረናል? ለመስጠት በቂ እንደሌላችሁ በተሰማችሁ ጊዜ አዳኙ ያበዛላችሁን አጋጣሚ ለማካፈል አስቡ።

ማቴዎስ 14፥22–33ቤተሰባችሁ በእነዚህ ጥቅሶች ላይ ያለውን ታሪክ መተወን ሊወዱ ይችላሉ። ደቀመዛሙርቱ ለምን ፍርሃት የተሰማቸው ይመስላችኋል? ጴጥሮስ ፍርሃቱን አሸንፎ ከጀልባው መውጣት የቻለው ለምንድነው? መስመጥ በጀመረ ጊዜ እንኳን እምነት ያሳየው እንዴት ነው? አንዳንድ ጊዜ እኛ እንደ ጴጥሮስ የምንሆነው እንዴት ነው?

ዮሐንስ 5፥1–16በእነዚህ ጥቅሶች ውስጥ “[መዳን]” የሚለውን ቃል ቤተሰባችሁ አባላት ልብ እንዲሉ ጋብዙ። ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን የሚያድነው በምን አይነት መንገድ ነው? እኛን ያዳነን መቼ እና እንዴት ነው ?

ዮሐንስ 6፥28–58ለእያንዳንዱ የቤተሰብ አባል የእንጀራ ቁራሽ ስጡ እናም ከእንጀራ እና ከሌሎች ጤናማ ምግቦች በምናገኘው ጥቅም ላይ ተወያዩ። ከዚያም ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ለምን “የህይወት እንጀራ” (ዮሐንስ 6፥35) እንዳለ በእነዚህን ጥቅሶች ላይ በአንድነት ፈልጉ። ህያው እንጀራን “መመገብ” ምን ማለት ነው? (ዲ. ቶድ ክርስቶፈርሰን “ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2017 (እ.አ.አ))፣ 36–39ን ተመልከቱ)።

ልጆችን ለማስተማር ተጨማሪ ሃሳቦችን ለማግኘት የዚህን ሳምንት ዝርዝርኑ፣ ተከተሉኝ—ለመጀመሪያ ክፍልን ይመልከቱ።

በሃሳብ የሚቀርብ መዝሙር “ጥበቡ እና ፍቅሩ እንዴት ታላቅ ነው፣” መዝሙሮች፣ ቁጥር 195።

የግል ጥናትን ማሻሻል

የራሳችሁን መንፈሳዊ ግንዛቤ ፈልጉ። በግል እና በቤተሰብ ጥናታችሁ በነዚህ የጥናት ዝርዝሮች ውስጥ ባሉ ጥቅሶች ራሳችሁን አትወሰኑ። ምናልባት እዚህ አጽንኦት ያልተሰጣቸው በነዚህ ምዕራፎች ውስጥ ጌታ ለናንተ መልዕክት ሊኖረው ይችላል። በጸሎት መንፈስ ፈልጓቸው።

ምስል
ኢየሱስ ጴጥሮስን ከውሃ ውስጥ እያወጣው

ከንፋሱ በተቃራኒ፣ በሊዝ ሌሞን ስዊንድል

አትም