2022 (እ.አ.አ)
መፅሐፈ ሞርሞን፣ መንፈሳዊ ጉዟችንን የሚመራ GPS (ጂፒኤስ)
ሚያዝያ 2022 (እ.አ.አ)


የአካባቢ መሪ መልእክት

መፅሐፈ ሞርሞን፣ መንፈሳዊ ጉዟችንን የሚመራ GPS (ጂፒኤስ)

GPS (ጂፒኤስ) ልንደርስባቸው ወደምንፈልጋቸው መዳረሻዎች እንደሚመራን፣ መፅሐፈ ሞርሞን ከሰማይ አባታችን ጋር ወደምናደርገው ግንኙነት እና ወደ መንፈስ ቅዱስ ወዳጅነት በሚወስድ መንገድ ላይ በየቀኑ ይመራናል።

ደቡብ አፍሪካ ውስጥ በኖርኩበት የቅርብ ጊዜ ሁለት ዓመት እና ጥቂት ወራት ውስጥ፣ ወደ ሁሉም የዕለት ተዕለት መዳረሻዎቼ እንድደርስ የሚረዳኝ መንገድ የመኖሩ አስፈላጊነትን ተማርኩኝ። ይህም GPS (ጂፒኤስ)፣ ከቤተሰብ ጋር የተገናኘ፣ ሙያዊ ግዴታዎች፣ ወይም የቤተክህነት ኃላፊነቶች ተግባሬን ለመወጣት እንድንቀሳቀስ ያስቻለኝ የኤሌክትሮኒክ ካርታ ነው።

ለዚህ የኤሌክትሮኒክ ካርታ ትኩረት ባደረግሁ ቁጥር፣ መድረሻዎቼን በሰዓቱ ደርሼ ወደ ቤተሰቤ በፍጥነት እመለሳለሁ። ነገር ግን፣ አደባባዩ ወይም መስቀለኛ መንገድ ሲያመልጠኝ፣ GPS (ጂፒኤስ) በጣም ረጅም መንገዶች ይወስደኛል እና አንዳንድ ጊዜ ወደ መድረሻዬ ለመድረስ እዘገይ ነበር—ወይም ወደ ሌላ የማላውቀው መድረሻ መንገድ ላይ ሙሉ በሙሉ እጠፋለሁ።

በዚህ ምድር ላይ እንደ ተጓዦች—በዚህ የሟች ህይወት ፈተናዎች ለመጓዝ እና ወደ ሰማያዊ ቤታችን ለመመለስ እንዲያስችለን—እግዚአብሔር የኢየሱስ ክርስቶስ ሌላ ቃል ኪዳን የሆነውን መጽሐፈ ሞርሞንን ሰጥቷል። ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመስማማት የመኖር ግባችንን እንድናሳካ ያስችለናል እናም ለሰማያዊ ርስታችን ያዘጋጀናል።

GPS (ጂፒኤስ) ልንደርስባቸው ወደምንፈልጋቸው መዳረሻዎች እንደሚመራን፣ መፅሐፈ ሞርሞን በየቀኑ ከሰማይ አባታችን ጋር ወደምናደርገው ግንኙነት እና ወደ መንፈስ ቅዱስ ወዳጅነት በሚወስድ መንገድ ላይ በየቀኑ ይመራናል። በየቀኑ ህይወታችንን በሚመራበት ጊዜ ይህን መጠቀም የእኛ ግዴታ ነው።

በሁሉም የእግዚአብሔር ልጆች ህይወት ውስጥ ባለው ዋጋ እና ጠቃሚ ሚና አንፃር፣ ፕሬዘደንት ራስል ኤም. ኔልሰን ከእያንዳንዳችን ጥልቅ ማሰላሰል የሚጠይቁ በርካታ ጥያቄዎችን ጠየቁ። እንዲህም አሉ፣ “ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ መፅሐፈ ሞርሞን ለእናንተ ምን ያህል ውድ ነው? አልማዝ ወይም ሩቢ ወይም መጽሐፈ ሞርሞን ቢሰጣችሁ የትኛውን ትመርጣላችሁ? በእውነትም፣ የትኛው ለእናንተ የሚበልጥ ዋጋ አለው?” 1

ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አለም አዳኝ እና ቤዛ ባላውቅ ኖሮ ህይወቴ ምን እንደሚመስል፣ እና በመፅሐፈ ሞርሞን ነቢያት እንዳስተማሩት እና በእኛ ዘመን በነቢዩ ጆሴፍ ስሚዝ በኩል በዳግም ከተመለሱት ሥርዓቶች እና ቃል ኪዳኖች ውጪ ምን እንደምሆን እንዳሰላስል የእርሳቸው ጥያቄዎች ፈቀዱልኝ።

ፕሬዘደንት ኔልሰን እንዲህ ቀጠሉ፦ “የእግዚአብሔር ልጅ ስለ እርሱ እና ስለሚወደው ልጁ የበለጠ ለማወቅ ሲፈልግ አንድ ኃይለኛ ነገር ይከሰታል። እነዚያ እውነቶች ከመፅሐፈ ሞርሞን የበለጠ በግልፅ እና በጉልበት የተማሩበት ቦታ የለም።” 2

ፕሬዘደንት ኔልሰን በቺሊ ያሉ መሪዎች እንዲያስቡባቸው ስለገፋፉት ስለሚከተሉት ሶስት ጥያቄዎች እንድታስቡ እፈልጋለሁ።

“መጀመሪያ፣ ያለ መጽሐፈ ሞርሞን ህይወታችሁ ምን ይመስል ነበር? ሁለተኛ፣ ምን የማታውቁት ነገር ይኖራል? ሦስተኛ፣ ምን አታገኙም ነበር?”

ፕሬዘደንት ኤዝራ ታፍት ቤንሰን እንዳሉት (1899–1994)፦ “መፅሐፈ ሞርሞን እግዚአብሔር ‘ምድርን አንድታጸዳት፣ . . . [ተመራጮቹን] ለመሰብሰብ’ ያዘጋጀው መሳሪያ ነው። ይህ ቅዱስ መጽሐፍ በስብከታችን፣ በትምህርታችን እና በሚስዮናዊነት ሥራችን የበለጠ ማዕከላዊ መሆን ያስፈልገዋል።

“በአሁኑ ጊዜ፣ መጽሐፈ ሞርሞን በየአራተኛው ዓመት በሰንበት ትምህርት ቤታችን እና በሴሚናሪ ክፍሎች ይጠናል። ይህ የአራት ዓመት ንድፍ ግን በቤተክርስቲያኗ አባላት በግል እና በቤተሰብ ጥናታቸው በኩል መከተል የለባቸውም። ‘ከየትኛውም መፅሐፍ በበለጠ በውስጡ ባሉት አዕምሮአዊ ትእዛዝ በመኖር ሰው ወደ እግዚአብሔር’ እንዲቀርብ ከሚያደርገው መጽሐፉ ገፆች ላይ በየቀኑ ማንበብ አለብን።’” 3

ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ መፅሐፈ ሞርሞንን በእውነተኛ ፍላጎት በሚያጠኑት ህይወት ውስጥ እውነተኛ ኃይል እና ተጽእኖ አለው። ለሚሻው ነፍስ ሰላምን ያመጣል፣ ቤቶችን እና ቤተሰቦችን በአንድነት ያገናኛል እናም በሰዎች መካከል ያለውን ግንኙነት በሁሉም ግንኙነቶች መሃል ላይ ሲቀመጥ በዳግም ያድሳል፣ ምክንያቱም ክርስቶስን በህዝቡ መካከል ስለሚያመጣ።

በአራተኛው ኔፊ፣ ምዕራፍ 1፣ ቁጥሮች 15 እስከ 18 ውስጥ እንደምናነበው፦

“እናም እንዲህ ሆነ በህዝቡ ልብ ውስጥ ባለው የእግዚአብሔር ፍቅር የተነሳ በምድሪቱ ፀብ አልነበረም።

“እናም ቅናት፣ ቁጣ፣ ሁከት፣ ዝሙት፣ መዋሸትም፣ ግድያም ሆነ ዝሙትን የሚቀሰቅስ ምንም ነገር አልነበረም፤ እናም በእርግጥ በእግዚአብሔር እጅ ከተፈጠሩት ሰዎች መካከል እንደዚህ ያለ ደስተኛ ሊሆን የቻለ ህዝብ አልነበረም።

“ሌቦችም ሆኑ ገዳዮች፣ ላማናውያንም ሆኑ ማንኛውም ዓይነት በመደብ የተለዩ ሰዎች አልነበሩም፤ ነገር ግን ሁሉም በአንድነት የክርስቶስ ልጆች፣ እናም የእግዚአብሔርንም መንግስት ወራሾች ነበሩ።

“እናም እነርሱ እንዴት የተባረኩ ነበሩ! ምክንያቱም ጌታ በስራዎቻቸው ሁሉ ባርኳቸዋልና፤ አዎን፣ አንድ መቶ አስረኛው ዓመት እስኪያልፍ እንኳን ተባርከዋል፤ በልፅገዋልም፤ እናም ከክርስቶስ ጉብኝት ጀምሮ የመጀመሪያው ትውልድ አልፎአልና፣ በምድሪቱ ሁሉ ፀብ አልነበረም።”

ከ35 ዓመታት በፊት መፅሐፈ ሞርሞንን ካገኘሁበት ጊዜ አንስቶ፣ በየቀኑ ማንበብ ቀጠልኩ እና እንደ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር ህይወቴ ትርጉም ያለው እየሆነ መጥቷል። ከሰማይ አባቴ እና ከባልንጀሮቼ ጋር ያለኝን ግንኙነት በግልፅ ተረድቻለሁ።

በቤተሰቤ ውስጥ ከልጆቻችን ጋር የመፅሐፈ ሞርሞን ጥናት እቅድ አለን። አሁንም በህይወታቸው ውስጥ እያሳየ ያለው ተፅዕኖ ትኩረት የሚስብ ነው እና በግልጽ የተረዱትን የወንጌል መሠረታዊ ሥርዓቶች ሲተገበሩ በማየታችን ደስተኞች ነን።

ኤሊ ኬ. ሞንጋ በሚያዝያ 2017 (እ.አ.አ) አካባቢ እንደ ሰባ ተመደበ። በኪንሻሳ፣ ኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ውስጥ ይኖራል። እሱ ከቪያኒ ሙዌንዜ ጋር የተጋባ ነው እናም የአራት ልጆች ወላጆች ናቸው።

ማስታወሻዎች

  1. ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “መጽሐፈ ሞርሞን፦ ያለ እሱ ህይወታችሁ ምን ሊሆን ይችላል?”፣ የጥቅምት 2017 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ።.

  2. ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “መጽሐፈ ሞርሞን፦ ያለ እሱ ህይወታችሁ ምን ሊሆን ይችላል?”።

  3. ኤዝራ ታፍት ቤንሰን፣ “Flooding the Earth with the Book of Mormon” [ምድርን በመፅሐፈ ሞርሞን መሸፈን]፣ የጥቅምት 1988 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ።

አትም