ኑ፣ ተከተሉኝ 2024 (እ.አ.አ)
አባሪ ሀ፦ ለወላጆች— ልጆቻችሁ ለእድሜልክ በእግዚአብሔር የቃል ኪዳን መንገድ ላይ እንዲሆኑ ማዘጋጀት


“አባሪ ሀ፦ ልጆቻችሁ ለእድሜልክ በእግዚአብሔር የቃል ኪዳን መንገድ ላይ እንዲሆኑ ማዘጋጀት፣” ኑ፣ ተከተሉኝ—ለቤት እና ለቤተክርስቲያን፦ ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 2025 (እ.አ.አ) [2025 ( እ.አ.አ)]

“አባሪ ሀ፣” ኑ፣ ተከተሉኝ—ለቤት እና ለቤተክርስቲያን፦ 2025 (እ.አ.አ)

ምስል
እናት እና ልጅ

አባሪ ሀ

ለወላጆች—ልጆቻችሁ በእድሜልክ በእግዚአብሔር የቃል ኪዳን መንገድ ላይ እንዲሆኑ ማዘጋጀት

እርሱ ስለሚወዳችሁ፣ ስለሚያምናችሁ እና ችሎታችሁን ስለሚያውቅ፣ የሰማይ አባት ልጆቻችሁን በእርሱ የቃል ኪዳን መንገድ ማለትም ወደ ዘለአለማዊ ህይወት ወደሚመራው መንገድ ውስጥ እንዲገቡ እና ቃል ኪዳናቸውን እንዲጠብቁ እንድትረዱ እድሉን ሰጥቷችኋል (ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 68፥25–28 ተመልከቱ)። ይህ የጥምቀት ቃል ኪዳንን እና በቤተመቅደስ ውስጥ የሚደረጉ ቃል ኪዳኖችን የመሳሰሉ ቅዱስ ቃል ኪዳኖችን ለማድረግ እና ለመጠበቅ እንዲዘጋጁ እነርሱን መርዳትን ያካትታል። በእነዚህ ቃል ኪዳኖች አማካኝነት ልጆቻችሁ እራሳቸውን ከአዳኙ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር በደስታ ለማጣበቅ ይችላሉ።

በቃል ኪዳኑ መንገድ ላይ ለሚያደርጉት ለዚህ ጉዞ ልጆቻችሁን ለማዘጋጀት ብዙ መንገዶች አሉ፣ እናም እነርሱን ለመርዳት የተሻለውን መንገድ እንድታገኙ የሰማይ አባት ይረዳችኋል። መነሳሳትን ስትሹ ትምህርቶች ሁሉ ለትምህርቶቹ በተያዘላቸው መርሃ ግብር መሠረት እንደማይከናወኑ አስታውሱ። በእርግጥ በቤት መማርን በጣም ኃይለኛ ከሚያደርገው ነገር መካከል በቀን ተቀን የህይወት ሂደት በተፈጥሮ የሚከሰት ዓይነት በምሳሌ እና በትንሽ ቀለል ባሉ የማስተማሪያ ወቅቶች የመማር እድል ነው። የቃል ኪዳን መንገድን መከተል ቀጣይነት ያለው የህይወት ሂደት እንደሆነ ሁሉ፣ ስለ ቃል ኪዳኑ መንገድ መማርም እንዲሁ ነው። (“ቤት እና ቤተሰብ፣” በአዳኙ መንገድ ማስተማር] [2022 (እ.አ.አ)]፣ 30–31 ተመልከቱ።)

ወደ ተጨማሪ መነሳሳት የሚያመሩ የተወሰኑ ሃሳቦች ከታች ቀርበዋል። ዕድሜያቸው በመጀመሪያ ክፍል ውስጥ የሆኑ ልጆችን ለማስተማር የሚሆኑ ተጨማሪ ሃሳቦችን አባሪ ለ ፦ ለመጀመሪያ ክፍል—ልጆችን ለእድሜልክ በእግዚአብሔር የቃል ኪዳን መንገድ ላይ እንዲሆኑ ማዘጋጀት ውስጥ ለማግኘት ትችላላችሁ።

ጥምቀት እና ማረጋገጫ

ወደ ቃል ኪዳን መንገድ “የምንገባበት በር፣ ንስሃ እና በውኃ መጠመቅ” (2 ኛ ኔፊ 31፥17) እንደሆነ ኔፊ አስተምሯል። ልጆቻችሁን ለጥምቀት እና ማረጋገጫ ለመቀበል እንዲዘጋጁ የመርዳት ጥረቶቻችሁ እግሮቻቸው በዛ መንገድ ላይ እንዲጸኑ ማድረግ ይችላሉ። እነዚህ ጥረቶች የሚጀምሩት በኢየሱስ ክርስቶስ ስለማመን እና ስለንስሃ በማስተማር ነው። እንዲሁም በየሳምንቱ ቅዱስ ቁርባንን በመካፈል የጥምቀት ቃል ኪዳኖቻችንን እንዴት እንደምናድስ ማስተማርን ያካትታሉ።

ምስል
ጥምቀት

ወደ ቃል ኪዳኑ መንገድ “የምንገባበት በር፣ ንስሃ እና በውኃ መጠመቅ” (2 ኛ ኔፊ 31፥17) እንደሆነ ኔፊ አስተምሯል።

ሊረዷችሁ የሚችሉ ግብዓቶች እነሆ፦ 2 ኔፊ 31፤ ስለ ጥምቀት የሚናገር የጓደኛ መጽሔት ልዩ ዕትም፤Topics and Questions [ርዕሶች እና ጥያቈዎች]፣ “ጥምቀት፣” የወንጌል ላይብረሪ።

  • በሰማይ አባት እና በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያላችሁን እምነት የሚያጠነክር ልምድ በሚኖራችሁ ጊዜ ሁሉ፣ ለልጃችሁ አካፍሉ። እምነት በእድሜልክ እየጠነከረ ሊሄድ የሚችል ነገር እንደሆነ እንዲገነዘቡ እርዷቸው። ልጃችሁ ከመጠመቁ በፊት በክርስቶስ ጠንካራ እምነት እንዲያዳብር ማድረግ የምትችሏቸው የተወሰኑ ነገሮች ምን ምን ናቸው?

  • ልጃችሁ የተሳሳተ ምርጫ ሲያደርግ፣ ስለ ንስሃ ስጦታ በደስታ ተናገሩ። እንዲሁም እናንተ የተሳሳተ ውሳኔ ካደረጋችሁ፣ ንስሃ ስትገቡ የሚመጣውን ደስታ አካፍሉ። ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሃጢያቶቻችን ስለተሰቃየ እና ስለሞተ በየቀኑ ንስሀ መግባት፣ ይቅር መባል እና የመለወጥን ሃይል ልንቀበል እንደምንችል መስክሩ። ልጃችሁ ይቅርታን ሲፈልግ፣ በነፃ እና በደስታ ይቅር በሉ።

  • ለልጃችሁ ስለጥምቀታችሁ ንገሩ። ፎቶዎችን አሳዩ እንዲሁም ትውስታዎችን አካፍሉ። እንዴት ተሠምቷችሁ እንደነበረ፣ የጥምቀት ቃል ኪዳኖቻችሁን መጠበቃችሁ እንዴት ኢየሱስ ክርስቶስን የበለጠ እንድታውቁት እንደረዳችሁ እና ቃል ኪዳኖቻች እንዴት ህይወታችሁን መባረክ እንደቀጠሉ ተናገሩ። ልጃችሁ ጥያቄዎችን እንዲጠይቅ አበረታቱ።

  • በቤተሰባችሁ ወይም በአጥቢያችሁ ውስጥ ጥምቀት ሲኖር፣ ልጃችሁ እንዲየይ ውሰዱት። እናንተ እና ልጃችሁ ስላያችኋቸው እና ስለተሰማችኋቸው ነገሮች ተነጋገሩ። ከተቻለ፣ ከሚጠመቀው ግለሰብ ጋር ተነጋገሩ እንዲሁም የሚከተሉትን ጥያቄዎች ጠይቁ፦ “ይህንን ውሳኔ የወሰንከው እንዴት ነው? የተዘጋጀኸው እንዴት ነው ?”

  • ልጃችሁ ለማድረግ ቃል የገባውን ነገር ሲያደርግ ስትመለከቱ፣ ልባዊ የሆነ አድናቆት ሥጡ። ቃል በገባናቸው ነገሮች መጽናት ስንጠመቅ የገባናቸውን ቃል ኪዳኖች ለመጠበቅ እንድንዘጋጅ እንደሚረዳን በመጠቆም አስታውቁ። ስንጠመቅ ለእግዚአብሔር የምንገባው ቃል ምንድን ነው? እርሱስ ምን ቃል ይገባልናል? (ሞዛያ 18፥8–10፣ 13 ተመልከቱ።)

  • ማረጋገጫ መቀበላችሁ እና የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን አባል መሆናችሁ እንዴት እንደባረካችሁ ተናገሩ። ሌሎችን ስላገለገላችሁ እና ሌሎች እናንተን ስላገለገሉ ወደ የሰማይ አባት እና ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መቅረብ የቻላችሁት እንዴት ነው? የቤተክርስቲያኗ አባል እንደመሆኑ ልጃችሁ ሌሎችን ለማገልገል እና ለማጠንከር የሚችልባቸውን መንገዶች እንዲያስብ እርዱት። ሌሎችን በማገልገል የሚገኘውን ደስታ እንዲለማመዱ እና እንዲያውቁት እርዷቸው።

  • እናንተ እና ልጃችሁ በጋራ የተቀደሠ ልምድ ሲኖራችሁ (ለምሳሌ በቤተክርስቲያን ውስጥ ቅዱሳት መጻህፍትን ስታነቡ ወይም አንድን ሰው ስታገለግሉ) ስለሚሰሟችሁ መንፈሳዊ ስሜቶች ወይም ስላገኛችኋቸው ግንዛቤዎች ንገሯቸው። ልጃችሁ ስለሚሰማው ነገር እንዲያካፍል ጋብዙት። ለእናንተ በግለሰብ ደረጃ የሚናገርባቸውን መንገዶች ጨምሮ መንፈስ ለሰዎች የሚናገርባቸውን የተለያዩ መንገዶች አስተውሉ። ልጃችሁ የመንፈስ ቅዱስን ተፅዕኖ ያየበትን ጊዜዎች እንዲያለይ እና እንዲያካፍላችሁ እርዱት።

  • በወንጌል ላይብረሪ ስብስቦች ውስጥ “እርሱን ስሙት!“ በሚል ርዕስ ስር ያሉትን የተወሰኑ ቪዲዮዎች በጋራ ተመልከቱ። የጌታ አገልጋዮች እርሱን ስለሚሰሙበት የተለያዩ መንገዶች ተነጋገሩ። ልጃችሁ የአዳኙን ድምፅ የሚሰማበትን መንገድ በሥዕል እንዲያስቀምጥ ወይም ቪዲዮ እንዲሰራበት ጋብዙት።

  • ቅዱስ ቁርባንን በቤተሰባችሁ ውስጥ የተቀደሰ እና አስደሳች ክስተት አድረጉት። በቅዱስ ቁርባን ወቅት በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ እንዴት እንደምታተኩሩ ለልጃችሁ አካፍሉት። ልጃችሁ ቅዱስ ቁርባን ለእርሱ ቅዱስ እንደሆነ ለማሣየት የሚችልበትን እቅድ እንዲያዘጋጅ እርዱት። ለምሳሌ፣ የቅዱስ ቁርባን ጸሎቶችን ቃላት ማዳመጥ የጥምቀት ቃል ኪዳኖቻችንን ያስታውሠናል።

  • ብዙ የጓደኛ መጽሔት እትሞች ልጆች ለጥምቀት እና ማረጋገጫ ለማግኘት እንዲዘጋጁ ለመርዳት የታሰቡ ፅሁፎችን፣ ታሪኮችን እና አክቲቪቲዎችን ያካትታሉ። ልጆቻችሁ የተወሰነውን መርጠው ከእናንተ ጋር እዲያነቡ እና እንዲደሰቱ አድርጉ። (በተጨማሪም በወንጌል ቤተ መጻህፍት የልጆች ክፍል ውስጥ “ለጥምቀት መዘጋጀት” በሚለው ስር ያሉትን ስብስቦች ተመልከቱ።)

የክህነት ሃይል፣ ሥልጣን እና ቁልፎች

ክህነት እግዚአብሔር ልጆቹን የሚባርክበት የእርሱ ስልጣን እና ኃይል ነው። የእግዚአብሔር ክህነት ዛሬ በምድር ላይ በኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይገኛል። ቃል ኪዳናቸውን የሚጠብቁ ሁሉም የቤተክርስቲያን አባላት—ሴቶች፣ ወንዶች እና ልጆች—በቤታቸው ውስጥ እራሳቸውን እና ቤተሰባቸውን ለማጠናከር በእግዚአብሔር የክህነት ኃይል ተባርከዋል (አጠቃላይ መመሪያ መጽሀፍ፦ በኋለኛው ቀን ቅዱሳን ቤተክርስቲያን ውስጥ ማገልገል3.6 ተመልከቱ)። ይህ ኃይል አባላት በግል እና በቤተሰቦቻቸው ህይወት ውስጥ የእግዚአብሔርን የደህንነት እና በዘለዓለም ህይወት ከፍ ከፍ የማድረግ ስራን ሲሰሩ ይረዳቸዋል (አጠቃላይ መመሪያ መጽሀፍ2.2 ተመልከቱ)።

ወንዶች እና ሴቶች በቤተክርስቲያን ጥሪዎች ውስጥ ሲያገለግሉ የክህነት ቁልፎችን በያዙ ሰዎች አመራር ስር በመሆን በክህነት ስልጣን አማካኝነት ያገለግላሉ። ሁሉም የሰማይ አባት ልጆች—ወንድ ልጆቹ እና ሴት ልጆቹ—ክህነትን የበለጠ ሲረዱ ይባረካሉ።

ሥርዓቶችን የምንቀበለው በክህነት ስልጣን አማካኝነት ነው። ብቁ የሆኑ ወንድ የቤተክርስቲያኗ አባላት ክህነትን በመሰጠት እና በክህነት ክፍሎች በመሾም የክህነት ሥልጣንን ይቀበላሉ (አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ3.4)። በክህነት ክፍሎች የተሾሙ ሠዎች፣ የክህነት ቁልፎችን በያዘ ሰው ሲፈቀድላቸው የክህነት ሥርዓቶችን ሊያከናውኑ ይችላሉ።

ስለክህነት የበለጠ ለመማር፣ ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “መንፈሳዊ ሀብቶች፣” ሊያሆና፣ ህዳር. 2019 (እ.አ.አ)፣ 76–79፤ ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “የክህነት ኃይል ዋጋ፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2016 (እ.አ.አ)፣ 66–69፤ “የክህነት መርሆዎች]፣” ምዕራፍ 3 በአጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ ውስጥ ተመልከቱ።

  • የክህነት ሥርዓቶችን ቀጣይነት ያላቸው የቤተሰባችሁ ህይወት ክፍሎች አድርጓቸው። ለምሳሌ፣ ልጃሁን በየሳምንቱ ለሚደረገው የቅዱስ ቁርባን ስብሰባ በመንፈስ እንዲዘጋጅ እርዱት። ልጃችሁ ሲታመም ወይም ማፅናኛ ወይም መመሪያ ሲያስፈልገው፣ የክህነትን በረከቶች እንዲሻ አበረታቱ። ጌታ በክህነት ኃይል አማካኝነት ቤተሰባችሁን እየባረከ ያለበትን መንገዶች መጥቀስን ልምድ አድርጉ።

  • ቅዱሳት መጻህፍትን በጋራ ስታነቡ፣ እግዚአብሔር ህዝቡን በኃይሉ አማካኝነት እንዴት እንደሚባርክ ለመወያየት እድሎችን ፈልጉ። እግዚአብሔር በክህነቱ አማካኝነት እናንተን የባረከበትን የራሳችሁን ልምድ አካፍሉ። በክህነት አማካኝነት ከእግዚአብሔር ስለምንቀበላቸው በረከቶች ምሳሌዎችን ለማግኘት አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ3.23.5 ተመልከቱ።

  • ከጥምቀት በኋላ ልጃችሁ የጥምቀትን ቃል ኪዳን በመጠበቅ የክህነት ኃይልን መቀበል እንደሚችል አስተምሩ። የፕሬዚዳንት ራስል ኤም. ኔልሰን መልዕክት የሆነውን “መንፈሳዊ ሀብቶች፣” (ሊያሆና፣ ህዳር 2019 (እ.አ.አ)፣ 76–79 ተመልከቱ) በጋራ ከልሱ። የክህነት ሥርዓቶች የእግዚአብሔርን ሃይል ወደ ህይወታችሁ እንዴት እንዳመጡ ለልጃችሁ ንገሩ። በክህነት ኃይል ስለተባረክንባቸው የተወሰኑ መንገዶች ዝርዝር ለማግኘት አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ3.5 ይመልከቱ።

  • “የጌታ አገልጋይ ምን ዓይነት ነው?” የሚለውን ጥያቄ ተወያዩበት። ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 121፥36–42 አንድ ላይ አንብቡና መልሶችን ፈልጉ። ልጆቻችሁ (ወይም ሌላ ሰው) በእነዚህ ጥቅሶች ውስጥ ካሉት አንዱን መርህ ወይም ባህርይ ተግባራዊ ሲያደርጉ ስትመለከቱ ወደ እነርሱ ጠቁሙ።

  • እናንተ ወይም ልጃችሁ በርን ለመክፈት ወይም መኪናን ለማስነሳት ቁልፍን ስትጠቀሙ፣ የክህነት መሪዎች ከያዙት ቁልፎች ጋር ለማነጸጸር የአፍታ ጊዜ ውሰዱ። (የክህነት ቁልፎችን ትርጉም ለማግኘት አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ3.4.1 ተመልከቱ)። የክህነት ቁልፎች ለእኛ “የሚከፍቱት” ወይም “የሚያስነሱት” ምንድን ነው? በተጨማሪም ጌሪ ኢ. ስቲቨንሰን፣ “የክህነት ቁልፎች እና ስልጣን የት ናቸው?፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2016 (እ.አ.አ)፣ 29፟–32፤ “ቁልፎቹ የት ናቸው?” (ቪዲዮ)፣ ወንጌል ላይብረሪ።

  • ለአንድ ጥሪ ስትለዩ የሚቻል ከሆነ ልጃችሁ እንዲገኝ ጋብዙ። ልጃችሁ ጥሪያችሁን ስትፈፅሙ እንዲያይ አድርጉ። ልጃችሁ ሊያግዛችሁ የሚችልበትን ተገቢ መንገዶች መፈለግም ትችላላችሁ። የጌታ ኃይል በጥሪያችሁ ውስጥ እንዴት እንደሚሰማችሁ ግለፁ።

ለቅድመ ዓያቶች መጠመቅ እና ማረጋገጫ መቀበል

ቤተመቅደሶች የሰማይ አባት ለልጆቹ ያለው ዕቅድ አካል ናቸው። በጌታ ቤት ውስጥ፣ ሁሉም ነገሮች ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ በሚጠቁሙት ቅዱስ ሥርዓቶች ስንሳተፍ ከሰማይ አባት ጋር ቅዱስ ቃል ኪዳኖችን እንገባለን። የሰማይ አባት፣ በዚህ ህይወት ሥርዓቶቹን ያልተቀበሉትን ጨምሮ ሁሉም ልጆቹ ቃል ኪዳኖችን እዲገቡ እና በሥርዓቶች እንዲሳተፉ መንገድ አመቻችቷል። ልጃችሁ 12 ዓመት በሚሆንበት የዓመቱ መጀመሪያ ላይ፣ በቤተመቅደስ ውስጥ ለሞቱ ቅድመ ዓያቶች ለመጠመቅ እና ማረጋገጫ ለመቀበል እድሜው በቂ ነው (በተጨማሪም 1 ቆሮንቶስ 15፥29 ተመልከቱ)።

  • ሁኔታችሁ በሚፈቅዱላችሁ ጊዜ ሁሉ ደጋግማችሁ ወደ ጌታ ቤት ሂዱ። ቤተመቅደስ ለምን እንደምትሄዱ እና ወደ ሰማይ አባት እና ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ለመቅረብ እንዴት እንደሚረዳችሁ ከልጃችሁ ጋር ተነጋገሩ።

  • የቤተመቅደስ መግቢያ ፈቃድ ጥያቄዎችን በጋራ ከልሱና ተወያዩባቸው። በለወጣቶች ጥንካሬ፦ ምርጫዎችን የማድረግ መመሪያ ከገፅ 36–37 ልታገኟቸው ትችላላችሁ። በቤተመቅደስ መግቢያ ፈቃድ ቃለ መጠይቅ ወቅት ስለሚሆነው ነገር ከልጃችሁ ጋር ተነጋገሩ። ለእናንተ የቤተመቅደስ መግቢያ ፈቃድ መያዝ ለምን አስፈላጊ እንደሆነ አካፍሉ።

  • ሚልክያ 4፥6ን በጋራ አንብቡ። ልቦቻችሁ ወደ ቅድመ ዓያቶቻችሁ እንዴት ሊመለሱ እንደሚችሉ ተናገሩ። የቤተሰብ ታሪካችሁን በFamilySearch.org ላይ በጋራ በመፈለግ ስለቅድመ ዓያቶቻችሁ የበለጠ ተማሩ። መጠመቅ እና ማረጋገጫ መቀበል የሚያስፈልጋቸውን የቅድመ ዓያቶችን ፈልጉ። የአጥቢያ የቤተመቅደስ እና የቤተሰብ ታሪክ አማካሪ ሊረዳችሁ ይችላል።

  • በወንጌል ላይብረሪ የልጆች ክፍል ውስጥ “ቤተመቅደስ” በሚለው ርዕስ ሥር ካሉት ስብስቦች ውስጥ የተወሰኑትን ግብዓቶች በጋራ ከልሱ። (በተጨማሪም “ለቤተመቅደስ ጥምቀቶች እና ማረጋገጫዎች ልጆቻችሁን ማዘጋጀት” የሚለውን በChurchofJesusChrist.org ውስጥ ተመልከቱ።)

የፓትርያርክ በረከትን መቀበል

የፓትርያርክ በረከት የምሪት፣ የመፅናናት እና የመነሳሳት ምንጭ ሊሆን ይችላል። ከሰማይ አባት ለእኛ የተሰጠ የግል ምክርን ይይዛል እንዲሁም ዘለአለማዊ ማንነታችንን እና ዓላማችንን እንድንገነዘብ ይረዳናል። የፓትርያርክ በረከቶችን ጠቀሜታ እና ቅዱስ ተፈጥሮ በማስተማር ልጃችሁ የፓትርያርክ በረከትን ለመቀበል እንዲዘጋጅ እርዱ።

የበለጠ ለመማር፣ Topics and Questions [ርዕሶች እና ጥያቄዎች]፣ “የፓትርያርክ በረከቶች፣” የወንጌል ላይብረሪ፤ ጁሊ ቢ. ቤክ፣ “You Have a Noble Birthright [የክብር በኩራት አላችሁ]፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2006 (እ.አ.አ)፣ 106–8 ተመልከቱ።

  • የፓትርያርክ በረከትን የመቀበል ልምዳችሁን ለልጃችሁ አካፍሉ። ለመቀበል እንዴት እንደተዘጋጃችሁ፣ የበለጠ ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ እንዴት እንደረዳችሁ እና በዚህ በረከት አማካኝነት እንዴት እናንተን መምራቱን እንደቀጠለ የመሳሰሉትን ነገሮች ልታካፍሉ ትችላላችሁ። ልጃችሁ የፓትርያርክ በረከትን ከተቀበሉ ከሌሎች የቤተሰብ አባላት ጋር እንዲነጋገር መጋበዝ ትችላላችሁ።

  • የሽማግሌ ራንዳል ኬ. ቤኔትን “Your Patriarchal Blessing—Inspired Direction from Heavenly Father [የፓትሪያርክ በረከታችሁ—ከሰማይ አባት የሚመጣ የተነሳሳ መመሪያ]” የተሠኘ መልዕክት እና የሽማግሌ ካዙሂኮ ያማሺታን “When to Receive Your Patriarchal Blessing [የፓትሪያርክ በረከታችሁን መቼ መቀበል እንደሚገባችሁ]” (ሊያሆና፣ ግንቦት 2023 (እ.አ.አ)፣ 42–43፣ 88–90) የተሠኘ መልዕክት አብራችሁ ከልሱ። የሰማይ አባት ለምን የፓትሪያርክ በረከትን እንድንቀበል እንደሚፈልግ ከእነዚህ መልእክቶች የተማራችሁትን አንዳችሁ ለሌላችሁ አካፍሉ። የፓትርያርክ በረከትን ስለመቀበል ሂደት ለማወቅ አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ18.17 ተመልከቱ።

  • የፓትርያርክ በረከቶችን የተቀበሉ የቅድመ ዓያቶች ካሏችሁ የተወሰኑትን ከልጃችሁ ጋር ማንበብ የሚያነሳሳ ሊሆን ይችላል። የሞቱ የቅድመ ዓያቶችን በረከቶች ለመጠየቅ ወደ ChurchofJesusChrist.org ግቡና በማሳያው ከላይ በስተቀኝ በኩል ያለውን Tools የሚለውን ተጫኑ ከዚያም የፓትርያርክ በረከቶች የሚለውን ምረጡ።

  • ልጃችሁ የፓትርያርክ በረከትን ከተቀበለ በኋላ፣ የተገኙ ማናቸውንም የቤተሰብ አባላት የተሰማቸውን ስሜት እንዲመዘግቡ ጋብዙ እናም ለልጃችሁ አጋሩ።

የቤተመቅደስ ቡራኬ መቀበል

እግዚአብሔር ሁሉንም ልጆቹን “ከላይ በሚመጣ ኃይል” ሊባርክ ይፈልጋል (ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 95፥8)። የግላችንን የቤተመቅደስ ቡራኬ ለመቀበል አንዴ ብቻ ወደ ቤተመቅደስ እንሄዳለን፣ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር የምናደርጋቸው ቃል ኪዳኖች እና እንደ ቤተመቅደስ ቡራኬ አካል የሚሰጠን መንፈሳዊ ኃይል በህይወታችን ውስጥ በየቀኑ ሊባርኩን ይችላሉ።

  • የቤተመቅደስን ምስል በቤታችሁ ውስጥ ስቀሉ። በጌታ ቤት ውስጥ የተሰማችሁን ስሜት ለልጃችሁ ንገሩ። ለጌታ እና ለቤቱ እንዲሁም እዚያ ስለገባችኋቸው ቃል ኪዳኖች ያላችሁን ፍቅር በተደጋጋሚ ለልጃችሁ ንገሩ። ለቅድመ ዓያቶቻችሁ ጥምቀትን ለማከናወን እና ማረጋገጫን ለመቀበል ከልጃችሁ ጋር ወደ ቤተመቅደስ የመሄድ እድሎችን ፈልጉ።

  • temples.ChurchofJesusChrist.orgን አብራችሁ አስሱ። About the Temple Endowment [ስለ ቤተመቅደስ ቡራኬ] እና Prepare for the House of the Lord [ለጌታ ቤት ተዘጋጁ] የመሠሉ ጽሁፎችን አብራችሁ አንብቡ። ልጆቻችሁ ስለቤተመቅደስ ያሏቸውን ማናቸውንም ጥያቄዎች እንዲጠይቁ አድርጉ። ከቤተመቅደስ ውጪ ስለምን ማውራት እንደምትችሉ ምሪት ለማግኘት የሽማግሌ ዴቪድ ኤ. ቤድናር መልዕክት የሆነውን “Prepared to Obtain Every Needful Thing [አስፈላጊ ነገሮችን ሁሉ ለመቀበል የተዘጋጁ]” (ሊያሆና፣ ግንቦት 2019፣ 101–4፤ በተለይም “Home-Centered and Church-Supported Learning and Temple Preparation [በቤት የተመሰረተ እና በቤተክርስቲያን የተደገፈ ትምህርት እና ለቤተመቅደስ መዘጋጀት]” ተመልከቱ)።

  • እናንተ እና ልጆቻችሁ በሥርዓቶች ውስጥ ስትሳተፉ ወይም ሌላ (እንደ ቅዱስ ቁርባን ወይም የፈውስ በረከት) ሥርዓቶችን ስትመለከቱ፣ በሥርዓቱ ውስጥ ስላለው ተምሣሌትነት ለመወያየት ጊዜ ውሰዱ። ምልክቶቹ ምንን ይወክላሉ? ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዴት ይመሰክራሉ? ይህ ልጃችሁ ስለኢየሱስ ክርስቶስ የሚመሰክሩ የቤተመቅደስ ሥርዓቶችን ተምሣሌታዊ ትርጉም ለማሰላሰል እንዲዘጋጅ ሊረዳው ይችላል።

  • ልጃችሁ በሞዛያ 18፥8–10፣ 13 የተገለፀውን የጥምቀት ቃል ኪዳን እየጠበቀ መሆኑን እንዲያስተውል እርዱት። እንዲሁም ጌታ ልጃችሁን እንዴት እየባረከው እንዳለ እንዲገነዘብ እርዱት። ልጃችሁ ቃል ኪዳኖችን ለመጠበቅ ያለውን ችሎታ መተማመን ገንቡ።

  • የቤተመቅደስ ቃል ኪዳኖቻችሁ ምርጫዎቻችሁን ስታደርጉ እንዴት እንደመሯችሁ እና ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንድትቀርቡ እንዴት እንደረዷችሁ በግልፅ እና በተደጋጋሚ ተናገሩ። በቤተመቅደስ ውስጥ የምንገባቸውን ቃል ኪዳኖች ለመከለስ፣ አጠቃላይ መመሪያ መጽሃፍ27.2ን መጠቀም ትችላላችሁ። የቤተመቅደስ ቡራኬን የተቀበላችሁ ከሆነ፣ የቤተመቅደስ ልብስ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የገባችሁትን ቃል ኪዳን ለማስታወስ እንዴት እንደሚረዳችሁ ለልጆቻችሁ ንገሩ (“Sacred Temple Clothing” [ቪዲዮ]፣ የወንጌል ላይብረሪ ውስጥ ተመልከቱ)።

በሚስዮን ማገልገል

ሽማግሌ ዴቪድ ኤ. ቤድናር እንዳስተማሩት፦ “ለማገልገል የምትዘጋጁበት በጣም ጠቃሚ የሆነው ነገር ቢኖር፣ ወደ ሚስዮን ከመሄዳችሁ ከረዥም ጊዜ በፊት ሚስዮናዊ መሆን ነው። … ጉዳዩ ወደ ሚስዮን መሄድ አይደለም፤ ከዚያ ይልቅ ጉዳዩ ሚስዮናዊ መሆን እና በመላ ህይወታችን ውስጥ በሙሉ ልባችን፣ ሃይላችን፣ አዕምሮአችን፣ እና ጥንካሬያችን ማገልገል ነው። … ለዕድሜ ልክ የሚስዮናዊ ስራ እየተዘጋጃችሁ ነው” (“Becoming a Missionary [ሚስዮናዊ መሆን]፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2005 (እ.አ.አ)፣ 45–46)። ልጃችሁ ሚስዮናዊ በመሆን ያገኛቸው ልምዶች ሚስዮናዊ በመሆን በሚያገለግልበት ጊዜ ብቻ ሳይሆን ለዘለዓለም ይባርከዋል።

የበለጠ ለመማር፣ ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “Preaching the Gospel of Peace [የሰላምን ወንጌል መስበክ]፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2022 (እ.አ.አ)፣ 6–7፤ ኤም. ራስል ባላርድ፣ “Missionary Service Blessed My Life Forever [የሚስዮን አገልግሎት ህይወቴን ለዘለአለም ባረከ]፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2022 (እ.አ.አ)፣ 8–10፤ Missionary Preparation: Adjusting to Missionary Life [ለሚስዮን ዝግጅት፦ ህይወትን ሚስዮን ወደመሆን ማስተካከል፣ ወንጌል ላይብረሪ ተመልከቱ።

  • ተፈጥሯዊ በሆኑ መንገዶች ወንጌልን በማካፈል ረገድ ምሳሌ ሁኑ። ስለሰማይ አባት እና ስለአዳኙ እንዲሁም ከአዳኙ ዳግም የተመለሰ ወንጌል እና የእርሱ ቤተክርስቲያን አባል በመሆናችሁ ስለተቀበላችኋቸው በረከቶች የሚሰማችሁን ስሜቶች ለሌሎች ለማካፈል ለሚገኙት እድሎች ሁሌም ንቁ ሁኑ። በቤተክርስቲያን እና ቤተሰብ ነክ በሆኑ አክቲቪቲዎች ላይ ሌሎች ሰዎች ከቤተሰባችሁ ጋር እንዲቀላቀሉ ጋብዙ።

  • ቤተሰባችሁ ከሚስዮናውያን ጋር መስተጋብር የሚፈጥሩበትን እድሎች ፈልጉ። ጓደኞቻችሁን እንዲያስተምሩ ጋብዟቸው ወይም በቤታችሁ ውስጥ ሰዎችን እንዲያስተምሩ ፍቀዱላቸው። ሚስዮናውያን ስላሏቸው ልምዶች እና የሚስዮናዊ አገልግሎት እንዴት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲቀርቡ እየረዳቸው እንደሆነ ጠይቋቸው። ሚስዮናዊ ለመሆን ለመዘጋጀት ምን እንዳደረጉ (ወይም ይህን አድርገን ቢሆን ኖሮ ብለው የሚመኟቸውን ነገሮች እንዳሉ) ጠይቋቸው።

  • በሚስዮን አገልግላችሁ የምታውቁ ከሆነ ስለልምዳችሁ በግልፅ እና በተደጋጋሚ ተናገሩ። ወይም በሚስዮን ያገለገሉ ጓደኞች ወይም የቤተሰብ አባላት እንዲናገሩ ጋብዙ። ወንጌልን በመላ ህይወታችሁ ለሌሎች ስላካፈላችሁባቸው መንገዶችም መናገር ትችላላችሁ። ልጃችሁ ወንጌልን የሚያካፍልባቸውን መንገዶች እንዲያስብ አግዙ።

  • ልጃችሁ የወንጌልን መርሆዎች ለቤተሰባችሁ እንዲያስተምር እድሎችን ስጡት። ልጃችሁ እምነቱን ለሌሎች ማካፈልም ይችላል። ለምሳሌ፣ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄዎችን መወያየት ትችላላችሁ፦ “ስለመጽሀፈ ሞርሞን ሰምቶ ለማያውቅ ሰው እንዴት ልናስተዋውቀው እንችላለን?” ወይም “ክርስቲያን ላልሆነ ሰው የአዳኙን አስፈላጊነት እንዴት መግለፅ እንችላለን?”

  • ልጃችሁ ከሰዎች ጋር በሚነጋገርበት ወቅት ምቾት የሚሰማው እንዲሆን አርዱ። ንግግርን ለመጀመር አንዳንድ መልካም መንገዶች ምን ምን ናቸው? ሌሎች የሚሉትን ለመስማት፣ በልባቸው ውስጥ ያለውን ለመረዳት እና ህይወታቸውን ሊባርኩ የሚችሉ የወንጌል እውነቶችን እንዴት ማካፈል እንደሚችል እንዲማር ልጃችሁን አበረታቱ።

  • ልጃችሁን ስለ ሌሎች ባህሎች እና እምነቶች ለማስተማር እድሎችን ፈልጉ። በሌሎች እምነቶች ውስጥ ያሉ መልካም እና ትክክለኛ መርሆዎችን እንዲገነዘብ እና እንዲያከብር እርዱ።

የእትመት ሥርዓትን መቀበል

በቤተመቅደስ ውስጥ ባል እና ሚስት ለዘለአለም መጋባት ይችላሉ። ይህ “እትመት” በሚባል ሥርዓት ውስጥ ይከናወናል። ምንም እንኳን ይህ ሥርዓት ለወንድ ወይም ሴት ልጃችሁ ከብዙ ዓመታት በኋላ የሚከናወን ቢሆንም፣ በእነዚያ ዓመታት ውስጥ በጋራ የምታደርጉት ትንሽ፣ ቀላል፣ ቀጣይነት ያላቸው ነገሮች ለዚህ አስደናቂ በረከት እንዲዘጋጁ ይረዳል።

  • ቤተሰብ፦ ለአለም የተላለፈ አዋጅን” አብራችሁ አንብቡ (የወንጌል ላይብረሪ)። በቤተሰብ ህይወት ውስጥ ስለሚገኝ ደስታ እና ስለውጤታማ ጋብቻ ይህ አዋጅ ምን ያስተምራል? በአዋጁ ውስጥ ከተጠቀሱት መርሆዎች አንዱን ከልጃችሁ ጋር ማጥናትን ምረጡ ። ከዚያ መርህ ጋር የሚዛመዱ የቅዱሳት መጻህፍት ጥቅሶችን በየቅዱሳት መጻህፍት መመሪያ ውስጥ ማየት ትችላላችሁ። ያንን መርህ በህይወታችሁ ውስጥ በይበልጥ ለመተግበር ግቦችን ማውጣትም ትችላላችሁ። ግቦቻችሁን ለማሣካት ስትሰሩ፣ ያንን መርህ መኖር በቤተሠባችሁ ህይወት ላይ ያለውን ተፅዕኖ በጋራ ተወያዩ።

  • In Praise of Those Who Save [የሚያድኑትን በማመስገን]” [ሊያሆና፣ ግንቦት 2016 (እ.አ.አ) 77–80] የተሠኘውን የፕሬዚዳንት ዲተር ኤፍ. ኡክዶርፍ መልዕክት ከልጃችሁ ጋር አንብቡ። “A Society of Disposables [ተጠቅሞ የሚጥል ህብረተሰብ]፣” ወደሚለው ርዕስ ስትደርሱ፣ በቤታችሁ ውስጥ ሊጣሉ የሚችሉ እና የማይቻሉ ነገሮችን መፈለግ ትችላላችሁ። ነገሮች ለረጅም ጊዜ እንዲቆዩ ስትፈልጉ እንዴት በተለየ መልኩ እንደምትንከባከቧቸው ተናገሩ። ጋብቻን እና የቤተሰብ ግንኙነቶችን ልንንከባከብ ስለሚገባን መንገድ ይህ ምን ይጠቁማል? ከፕሬዚዳንት ኡክዶርፍ መልዕክት አዳኙ ጠንካራ ጋብቻን እና ቤተሰቦችን ለመገንባት ሊረዳን ስለሚችልበት መንገድ ሌላ ምን እንማራለን?

  • እናንተ እና የትዳር አጋራችሁ ክርስቶስን ማዕከል ስላደረገ ዘለአለማዊ የጋብቻ ጥምረት ይኖራችሁ ዘንድ እየተማራችኋቸው ስላሉት ነገሮች እና ለማሻሻል እየጣራችሁ ስላላችሁባቸው መንገዶች ለልጃችሁ በግልጽ ተናገሩ። እናንተ እና የትዳር አጋራችሁ በቤተመቅደስ ውስጥ የታተማችሁ ከሆነ፣ ከጌታ ጋር የገባችሁትን ቃል ኪዳን ለመጠበቅ እንዴት እንደምትጥሩ ለልጃችሁ በምሳሌ አሳዩ። የሰማይ አባትን እና አዳኙን የግንኙነታችሁ ማዕከል ለማድረግ እንዴት እንደምትጥሩ እና እንዴት እየረዷችሁ እንደሆነ ለልጃችሁ ንገሩ (በተጨማሪም፣ ዩሊሰስ ሶሬስ፣ “In Partnership with the Lord [ከጌታ ጋር በመተባበር]፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2022 (እ.አ.አ)፣ 42–45 ተመልከቱ)።

  • የቤተሰብ ውሳኔዎችን ማድረግ ሲያስፈልግ፣ የቤተሰብ ምክር ቤት ፍጠሩ ከዚያም ውይይት አድርጉ። የሁሉም የቤተሰብ አባላት ሃሳቦች እንደተደመጡ እና ዋጋ እንደተሰጣቸው አረጋግጡ። ምንም እንኳን ሁሉም ሰው ነገሮችን በተመሳሳይ መንገድ ባይመለከትም፣ እነዚህን ውይይቶች በቤተሰብ ግንኙነት ውስጥ ጤናማ የሐሳብ ልውውጥ እና ደግነትን ለማሳየት እንደ እድል ተጠቀሙ። (ኤም. ራስል ባላርድ፣ “Family Councils [የቤተሰብ ምክር ቤቶች]፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2016 (እ.አ.አ)፣ 63–65ን ተመልከቱ።)

  • በቤተሰብ ውስጥ አለመግባባት ወይም ግጭት ሲኖር፣ ትህትናን እና ርህራሄን አሳዩ። ልጃችሁ ግጭትን በክርስቶስ መሰል መንገዶች መፍታት እንዴት ለደስተኛ ትዳር እንዲዘጋጅ ሊረዳው እንደሚችል እንዲያይ እርዱት። ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 121፥41–42ን አብራችሁ አንብቡ፣ ከዚያም በእነዚህ ጥቅሶች ውስጥ ያሉ መርሆዎች እንዴት በትዳር ላይ ተግባራዊ እንደሚሆኑ ተነጋገሩ።

አትም