አጠቃላይ ጉባኤ
አድምጡት
የሚያዝያ 2020 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ።


አድምጡት

በጥርጣሬ እና በፍርሃት በተከበብን ጊዜ፣ ​​ከሁሉም በላይ በጣም የሚረዳን ልጁን መስማት እንደሆነ የሰማይ አባታችን ያውቃል።

ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ በዚህ እሁድ ጠዋት በቴክኖሎጂ ምክንያት ለማምለክ አብረን ለመገናኘት በመቻላችን እንዴት ምስጋና ይሰማኛል። የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በምድር መመለሱን በማወቅም እንዴት የተባረክን ነን!

ባለፉት ሳምንታት ውስጥ፣ በግል ህይወታችን ላይ ብዙዎቻችን መተራመስ መጥተውብናል። የምድር መንቀጥቀጥ፣ እሳት፣ ጎርፍ፣ ወረርሽኝ፣ እና የነዚህ ውጤቶች በየጊዜ የምናደርጋቸውን ነገሮች አተራምሰዋል እናም የምግብ፣ የአስፈላጊ ነገሮች እና የቁጠባዎች እጥረት እንዲከሰት አድርገዋል።

በዚህ ሁሉ መካከል፣ ለአጠቃላይ ጉባኤ ከእኛ ጋር በመሆን ሁከት በነገሠበት በዚህ ወቅት የጌታን ቃል ለመስማት በመምረጣችሁ እናሞግሳችኋለን እንዲሁም እናመሰግናለን። ከመከራ ጋር ተያይዞ የሚጨምር ጨለማ የኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃን ሁልጊዜ በብሩህነት እንዲያበራ ያደርጋል። በዚህ በአለማዊ ሁካታ እያንዳንዳችን ማድረግ ስለምንችላቸው መልካም ነገሮች አስቡባቸው። በአዳኝ ያላችሁ ፍቅር እና እምነት የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ሙላት ዳግም መመለስን ለማግኘት ለሰው የሚረዳም ሊሆን ይችላል።

ባለፉት ሁለት አመታት ውስጥ፣ እህት ኔልሰን እና እኔ ብዙ ሺህ የሆናችሁትን በአለም በተለያዩ ቦታዎች ሁሉ ተገናኝተናል። በውጪ መሰብሰቢያዎች እና በሆቴል መሰብሰቢያ ቦታዎችም ተሰባስበናል። በእያንዳንዱ ቦታዎችም፣ በጌታ ከተመረጡት መካከል እንደሆንኩኝ እና በአይኖቼ ፊት የእስራኤል መሰብሰብ እየደረሰ እያየሁኝ እንደሆነ ተሰምቶኛል።

“የቀደሙት አባቶቻችን በጉጉት በጠበቋቸው” ቀን ውስጥ እየኖርን ነን።1። ነቢዩ ኔፊ በራዕይ ብቻ ያየውን፣ እኛም በመጀመሪያው መቀመጫ ተቀምጠን ይህን በህይወት እየተመለከትን ነን፣ በቤተክርስቲያን ቅዱሳንና በምድር ገፅ ላይ ሁሉ በተበተኑት የጌታ የቃልኪዳን ህዝቦች ላይ የእግዚአብሔር በግ ኃይል ሲወርድ ተመለከትኩ፤ እነርሱም ፅድቅንና የእግዚአብሔርን ኃይል በታላቅ ክብር የታጠቁ ነበሩ።”2

እናንተ፣ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ ኔፊ ካያቸው ከእነዚያ ወንዶች፣ ሴቶች እና ልጆች መካከል ናችሁ። አስቡበት!

የትም ብትኖሩ እናም ሁኔታችሁም ምንም ቢሆኑ፣ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የእናንተ አዳኝ ነው፣ እናም የእግዚአብሔር ነቢይ፣ ዮሴፍ ስሚዝ፣ የእናንተ ነቢይ ነው። ከቅዱሳን “ምንም ነገር ሊከለከል በማይችልበት”3 የዚህ የመጨረሻ ጊዜ ዘመን ነቢይ እንዲሆን እርሱ ምድር ከመመስረቷ አስቀድሞ የተቀባ ነበር። በዚህ በሂደት ላይ ባለው የዳግም መመለስ ወቅት ራእይ ከጌታ መምጣቱን ቀጥሏል።

የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በዳግም መመለሱ ለእናንተ ምን ትርጉም አለው?

ይህም ማለት እናንተ እና ቤተሰቦቻችሁ በጋራ ለዘለአለም ለመተሳሰር ትችላላችሁ ማለት ነው። ይህ ከኢየሱስ ክርስቶስ ባለ ሥልጣን በመጠመቃችሁ እና እንደ እርሱም ቤተክርስቲያን አባልነት ስለተረጋገጣችሁ፣ የመንፈስ ቅዱስን የማያቋርጥ የጠበቀ ወዳጅነት ልትደሰቱ ትችላላችሁ ማለት ነው። እርሱም ይመራችኋል እናም ይጠብቃችኋል። ያም ማለት እርሱ ያለመፅናኛ እናም እርዳታ ከሚሰጣችሁ ከእግዚአብሔር ሀይል ግንኙነት ሳይኖራችሁ አይተዋችሁም። ይህም አስፈላጊ ስርዓቶችን ስትቀበሉ እና ከእግዚአብሔር ጋር ቃል ኪዳን ስትገቡና ስታከብሯቸው የክህነት ሀይል ሊባርካችሁ ይችላል ማለት ነው። በተለይም በእነዚህ አውለ ንፋሱ በሚናወጥበት ጊዜ፣ እነዚህ እውነታዎች ለነፍሳችን ምን አይነት መልህቅ ነው።

መፅሐፈ ሞርሞን የሁለት ታላላቅ ስልጣኔዎች መነሳት እና መውደቅ ታሪክ ይነግራል፡፡ ከህዝብ አብዛኛዎች እግዚአብHኤርን ለመርሳት፣ የጌታ ነቢያትን ማስጠንቀቂያ ለማስወገድ፣ እና ሀይልን፣ ታዋቂነትን፣ እና የስጋዊ ደስታዎችን ለመፈለግ እንዴት ቀላል እንደሆነ የእነርሱ ታሪክ ያሳያል፡፡4 በተደጋጋሚም፣ የጥንት ነቢያት “ታላቅ እና አስደናቂ ነገሮችን ለህዝቡ” አውጀዋል፣ “[ብዙዎቹም] አላመኑም፡፡”5

ይህ በጊዜአችን የተለየ አይደለም፡፡ በአመታት ውስጥ፣ ታላቅ እና አስደናቂ ነገሮች በምርድ ዙሪያ በሚገኙ መስበኪያዎች ተሰምተዋል፡፡ ግን አብዛኛዎቹ ህዝቦች እነዚህን እውነቶች አይቀበሉም፣ ምክንያቱም እነዚህን የት እንደሚያገኙ ባለማወቃቸው፣6 ወይም ሙሉ እውነትን የሌላቸውን ስለሚያዳምጡ፣ ወይም የአለምን ነገር ለመከተል ብለው እውነትን በመቃወማቸው ነው።

ጠላት ብልህ ነው። ለሺህ አመታት፣ እርሱ መልካምን ክፉ እና ክፉውን መልካም እያስመሰለ ነው።7 መልእክቱም የጎላ፣ ደፋር እና ኩራተኛ ነው።

ይህም ቢሆን፣ ከሰማይ አባታችን የሚመጣው መልእክት በጣም የተለየ ነው። እርሱ የሚያነጋግረው በቀላል፣ በጸጥተኛ፣ እና በሚያስደንቅ ሁኔታ ግልፅ ሆኖ ግራ ለመጋባት በማንችልበት መንገድ ነው።8

ለምሳሌ፣ በምድር ላይ ለሚኖሩት ሟቾች አንድያ ልጁን በሚያስተዋውቅበት ጊዜ፣ ይህን ያደረገው በሚያስገርም ጥቂት ቃላት ነው። በመቀየሪያ ተራራ ላይ ለጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ እና ዮሀንስ፣ እግዚአብሔር እንዲህ አለ፣ “የምወደው ልጄ ይህ ነው፣ እርሱን ስሙት።”9 በጥንት ለጋስ ምድር ውስጥ ለነበሩት ኔፋውያን ቃላቶች እንዲህ ነበሩ፣ “እነሆ በእርሱ ደስ የሚለኝ፤ ስሜንም ያከበርኩበት፣ የምወደው ልጄ ይህ ነው—እርሱን ስሙት።”10 እናም ለጆሴፍ ስሚዝ፣ ይህን የዘመን ፍጻሜ በተከፈተበት ግርማዊ ማወጃ፣ እግዚአብሔር በቀላል እንዲህ አለ፣ “ተናገረኝ—የምወደው ልጄ ይህ ነው። እርሱን ስማው!11

አሁን ውድ ወንድሞቼ እና እህቶቼ፣ ቀደም ሲል በተጠቀሱት በእነዚህ ሦስት ጊዜዎች፣ አብ ወልድ ከማስተዋወቁ በፊት፣ የተሳተፉት ሰዎች በፍርሀት ውስጥ ነበሩ እና በተወሰነ ደረጃ ደግሞ ተስፋ ቢስ መሆናቸውን አስቡ።

ሐዋሪያት ኢየሱስ ክርስቶስ በመቀየሪያ ተራራ ላይ በዳመና ተከቦ ሲያዩት ፈርተው ነበር።

ኔፋውያን ለብዙ ቀናት በደረሰባቸው መደምሰስ እና በጭለማ ምክንያት ፈርተው ነበር።

ዮሴፍ ስሚዝም ሰማያት ከመከፈታቸው በፊት በጭለማ ሀይል ስር ነበር።

የሰማይ አባታችን በጥርጣሬ እና በፍርሃት በተከበብን ጊዜ፣ ​​ከሁሉም በላይ በጣም የሚረዳንን ልጁን መስማት እንደሆነ ያውቃል።

ምክንያቱም የእርሱን ልጅ ለመስማት፣ በእውነት ለመስማት ስንሻ፣ በማንኛውም ሁኔታ ምን ማድረግ እንዳለብን ለማወቅ እንመራለን።

በትምህርት እና ቃል ኪዳን ውስጥ የመጀመሪያው ቃል አድምጡ፣ የሚለው ነው።12 ይህም ማለት “ታዛዥ ለመሆን ባለ ፍላጎት መስማት ነው።”13 ማድመጥ ማለት “እርሱን መስማት”፥ አዳኝ የሚለውን ማድመጥ እና ከዚያም የእርሱን ምክር መከተል ነው። “እርሱን አድምጡ” በሚሉት በእነዚያ ሁለት ቃላት፣ እግዚአብሔር ለዚህ ህይወት ውጤታማነት፣ ደስታ፣ እና ሀሴት ንድፍ ሰጥቶናል። የጌታን ቃል መስማት አለብን፣ እነርሱንም ማድመጥ እና እርሱ የነገረንን መከተል አለብን፡፡

እንደ ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት፣ እሱን ለመስማት የምናደርገው ጥረት ሁልጊዜ የበለጠ የታሰበ መሆን አለበት። የዕለት ተዕለት ሕይወታችንን በቃሉ፣ ትምህርቶቹ፣ በእውነቶቹ ለመሙላት ንቁ እና ወጥ የሆነ ጥረት ይጠይቃል።

እኛ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በምናገኘው መረጃ ላይ ብቻ መተማመን አንችልም፡፡ በኢንተርኔት ላይ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ቃላት እና በጩኸት በተሞላው ዓለም ውስጥ ጫጫታ ባላቸው የጠላቶች ጥረት፣ እሱን ለመስማት የት መሄድ እንችላለን?

ወደ ቅዱሳት መጻህፍት ለመሄድ እንችላለን፡፡ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እና ስለ ወንጌል፣ የኃጢያት ክፍያ ታላቅነት፣ እና የአባታችን ታላቅ የደስታ እና ቤዛነት እቅድ ያስተምሩናል። በእነዚህ ረብሻ በሚበዛባቸው ቀናት፣ ለመንፈሳዊ ደህንነት በእግዚአብሄር ቃል ውስጥ በየቀኑ መጥለቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በየእለቱ የክርስቶስን ቃላት በምንመገብበት ጊዜ፣ ​​ያጋጥመናል ብለን ላላሰብናቸው ችግሮች እንዴት ምላሽ እንደምንሰጥ የክርስቶስ ቃሎች ይነግሩናል፡፡

ደግሞም በቤተመቅደስ ውስጥም እርሱን ለመስማት እንችላለን፡፡ የጌታ ቤት የመማሪያ ቤት ነው። በዚያም፣ ጌታ በእርሱ መንገድ ያስተምራል። በዚያም፣ እያንዳንዱ ስርዓቶች ስለአዳኝ ያስተምራሉ። በዚያም መጋረጃውን እንዴት መቅደድ እና ከሰማይ ጋር በጣም ግልፅ በሆነ ሁኔታ እንደምንገናኝ እንማራለን። በዚያም፣ ጠላትን እንዴት መገሰጽን እና እኛን እና የምንወዳቸውን ለማጠናከር የጌታ ክህነት ሀይል ለመቀበል እንደምንችል እንማራለን። እያንዳንዳችን ወደዚያ ለመጠለል ምን ያህል ጉጉት ያድርብናል፡፡

እነዚህ ጊዜያዊ COVID-19 ገደቦች ሲነሱ፣ እባክዎን በቤተመቅደስ ለማምለክ እና ለማገልገል መደበኛ ጊዜ መድቡ። የዚያ እያንዳንዱ ደቂቃ ማንም ነገር ሊያደርገው በማይችሉበት መንገድ እርስዎን እና ቤተሰብዎን ይባርካቸዋል። በዚያ በምትገኙበትም ጊዜ የምትሰሙትን እና የሚሰማችሁን ለማሰላሰል ጊዜ ውሰዱ። ሕይወታችሁን እና የምትወዷቸውን እና የምታገለግሏቸውን ሰዎች ሕይወት ለመባረክ ሰማይን እንዴት እንደሚከፍቱ ጌታ እንዲያስተምራችሁ ጠይቁት።

በቤተመቅደስ ውስጥ ማምለክ በአሁኑ ጊዜ የማይቻል ቢሆንም፣ የቤተሰብ ታሪክ ጥናት እና ማውጫዎችን ጨምሮ በቤተሰብ ታሪክ ውስጥ ያላችሁን ተሳትፎ እንዲጨምሩ እጋብዛችኋለሁ። በቤተመቅደስ እና በቤተሰብ ታሪክ ስራ ጊዜአችሁን ስታሳልፉ፣ እሱን ለመስማት ችሎታዎቻችሁ እንደሚጨምሩ እና እንደሚሻሽሉ ቃል እገባለሁ።

የመንፈስ ቅዱስን ሹክሹክታ ለማወቅ ያለንን ችሎታ ስናሳድግ፣ በግልፅ እርሱን ለመስማት እንችላለን። መንፈስን እንዴት እንደሚነግርዎት ማወቅ ከአሁን ይበልጥ አስፈላጊ ሆኖ አያውቅም። በስላሴ ዘንድ፣ መንፈስ ቅዱስ መልእክተኛ ነው። አብ እና ወልድ እንዲኖራችሁ የሚፈልጉትን ሀሳቦች ወደ አዕምሮአችሁ ያመጣል። እርሱ አፅናኝ ነው። የሰላም ስሜት ወደ ልባችሁ ያመጣል። ስለእውነት ይመሰክራል እናም የጌታን ቃል ስትሰሙ እና ስታነቡም እውነት የሆነውንም ያረጋግጣል።

የግል ራዕይን ለመቀበል መንፈሳዊ አቅማችሁን ለመጨመር የሚፈልገውን ማንኛውንም ነገር እንዲያደርጉ ያለኝን ምልጃዬን አድሳለሁ።

እንዲህ ማድረግ በሕይወታችሁ ውስጥ እንዴት እንደሚራመዱ፣ በችግር ጊዜ ምን ማድረግ እንዳለባችሁ፣ እና የጠላትን ፈተናዎች እና ማታለያዎች እንዴት መለየት እና ማስወገድ እንደሚቻል ለማወቅ ይረዳችኋል።

እናም በመጨረሻም፣ እርሱን የምንሰማው የነቢያትን፣ የባለራዕያትን፣ እና የገላጮችን ቃላት በማክበር ነው። የኢየሱስ ክርስቶስ የተሾመ ሐዋሪያት ስለእርሱ ሁልጊዜም ይመሰክራሉ። ልብ በሚያንጠለጥለው በሟች ልምዶቻችን ውስጥ ስንጓዝ መንገዱን ያመለክታሉ።

አዳኙ የተናገረውን፣ እና አሁን በነቢያቱ በኩል የሚናገረውን ሆን ብለን በበለጠ ለመስማት፣ ለማድመጥ እና ለማክበር ስንጥር ምን ይደርሳል? ፈተናን፣ ትግልን እና ድክመትን ለመቋቋም ተጨማሪ ኃይል እንደሚባርኳችሁ ቃል እገባለሁ። በጋብቻችሁ፣ በቤተሰቦቻችሁ ግኑኝነቶች፣ እና በየዕለቱ ስራዎቻችሁ ተዓምራትን እንደምታገኙ ቃል እገባላችኋለሁ። እናም ምንም እንኳን በህይወታችሁ ውስጥ ሁካታ ቢጨምር እንኳን ደስታን የመሰማት አቅማችሁ እንደሚጨምር ቃል እገባለሁ።

ይህ የሚያዝያ 2020 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ ዓለምን የለወጠ አንድ ክስተት የምናከብርበት ጊዜያችን ነው፡፡ ይህንን የጆሴፍ ስሚዝ የመጀመሪያ ራዕይን 200ኛ ዓመት ስናከብር፣ የቀዳሚ አመራር እና የአስራ ሁለቱ ሐዋሪያት ምክር ቤት እኛ ይህንን የመታሰቢያ በዓል በተገቢ ሁኔታ ለማክበር ምን ማድረግ እንደምንችል አሰላስለናል።

ይህም መገለጥ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በሙሉነት ዳግም እንዲመለስ እና በዘመኑ ፍፃሜ ጊዜ ውስጥ በሙሉነት እንዲመጣ አስጀምሯል።

አንድ የመታሰቢያ ሐውልት ማቆም እንዳለብን አሰብን። ነገር ግን የዚያ የመጀመሪያውን ራእይ ልዩ ታሪክ እና አለም አቀፍ ተፅእኖን ስንመለከት፣ የመታሰቢያ ሃውልትን ለመትከል አሰብን፣ ይህም የእምነ በረድ ወይም የድንጋይ ሳይሆን፣ የቃላት ነው፣ እነዚህም የክብር እና የተቀደሰ አዋጅ ቃሎች ናቸው፣ እነዚህም “በድንጋይ ታቦት” ላይ የሚቀረጹ ሳይሆን በልባችን “ስጋዊ ታቦት” ላይ የሚጻፉ ናቸው።14

ቤተክርስቲያኗ ከተደራጀች ጀምሮ፣ አምስት አዋጆች ብቻ ተሰጥተዋል፣ የመጨረሻው በ 1995(እ.ኤ.አ) በፕሬዚዳንት ጎርደን ቢ ሂንክሊይ የቀረበው “ቤተሰብ-ለአለም አዋጅ” የሚለው ነው።

አሁን በዓለም ታሪክ ውስጥ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠውን ይህንን ጊዜ እና እስራኤልን ለኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምፅዓት ለማዘጋጀት ጌታ የሰጠውን ሀላፊነት ስናስብ፣ እኛ የቀዳሚ አመራሮች እና የአስራ ሁለቱ ሐዋሪያት ጉባኤ የሚከተሉትን አዋጆች እናወጣለን፡፡ ርእሱም እንዲህ የሚል ነው፣ “የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ሙላት ዳግም መመለስ፤ የሁለት ምእተ አመታት መታሰብያ ለአለም የተላለፈ አዋጅ።” በኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስትያን ቀዳሚ አመራር እና አስራ ሑለት ሐዋሪያት ሸንጎ የተጻፈ ነው። ቀኑም ሚያዚያ 2020 (እ.ኤ.አ) ለዛሬ ለመዘጋጀት፣ ዮሴፍ ስሚዝ መጀመሪያ አብን እና ወልድን ባየበት በተቀደሰው ዛፎች ውስጥ ይህንን አዋጅ ቀድቼዋለሁ፡፡

“በአለም ውስጥ የሚገኙትን እያንዳንዱን ህዝብ እግዚአብሔር ልጆቹን እንደሚወድ በአክብሮት እናውጃለን። እግዚአብሔር አብ የተወደደ የልጁ የኢየሱስ ክርስቶስን መለኮታዊ ልደት፣ ተወዳዳሪ የሌለው ሕይወት፣ እና የማያልቀውን ቤዛዊ መሥዋዕትነት ሰጠን። በአብ ኃይል፣ ኢየሱስ እንደገና ተነስቶ በሞት ላይ ድል ተቀዳጅቷል፡፡ እሱ አዳኛችን፣ ምሳሌያችን እና ቤዛችን ነው፡፡

“ከሁለት መቶ ዓመታት በፊት፣ በ 1820(እ.ኤ.አ) ውብ በሆነ የፀደይ ጠዋት ላይ ወጣቱ ዮሴፍ ስሚዝ የትኛውን ቤተክርስቲያን ለመቀላቀል ለማወቅ በመፈለግ በኒው ዮርክ፣ ዩናይትድ ስቴትስ በሚገኘው ቤቱ አቅራቢያ ለመጸለይ ወደ ጫካ ገባ። የነፍሱን መዳን በተመለከተ ጥያቄዎች ነበሩት እናም እግዚአብሔር እንደሚመራው ይተማመን ነበር፡፡

“ለእርሱ ጸሎት ምላሽ፣ እግዚአብሔር አብ እና ልጁ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ለጆሴፍ እንደተገለጡ እና መጽሐፍ ቅዱስ እንደተነበየው (የሃዋሪያት ስራ 3፥21) ‘የሁሉንም ነገሮች መልሶ መታደስ’ እንደመረቁ በትህትና እናውጃለን። በዚህ ራእይ ውስጥም፣ የቀደሙት ሐዋርያት ሞት ተከትሎ፣ የክርስቶስ የአዲስ ኪዳኗ ቤተክርስቲያን ከምድር እንደጠፋች ተማረ፡፡ ዮሴፍ ይህንንም መልሶ በመምጣት ደረጃ ትልቅ ሚና ይጫወታል።

“በአብ እና በወልድ አመራር፣ የሰማይ መልእክተኞች ጆሴፍን ለማስተማር እና የኢየሱስ ክርስቶስን ቤተክርስቲያን እንደገና ለማቋቋም እንደመጡ እናረጋግጣለን፡፡ ለኃጢያት ስርየት ሙሉ በሙሉ በመጥለቅ ለማጥመቅ ከሞት የተነሳው መጥምቁ ዮሐንስ የጥምቀት ስልጣንን መልሷል። ከመጀመሪያዎቹ አስራ ሁለት ሐዋሪያት ሦስቱ፣ ማለትም ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ እና ዮሐንስ የክህነት ስልጣን ሀላፊነቶችን እና ቁልፎችን እንደገና አድሰዋል፡፡ ከሞት በሚዘልቅ ዘላለማዊ ግንኙነቶች ቤተሰቦችን ለዘላለም አብረው እንዲገኛኙ የማድረግ ስልጣንን መልሶ የሰጠው ኤልያስን ጨምሮ ሌሎችም መጡ፡፡

“ዮሴፍ ስሚዝ የጥንት መዝገብ የሆነውን መፅሐፈ ሞርሞን፤ ሌላኛው የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክርን ለመተርጎም የእግዚአብሔር ስጦታ እና ሀይል እንደተሰጠው በተጨማሪ እንመሰክራለን። የዚህ ቅዱስ ጽሑፍ ገጾች ከትንሳኤው በኋላ ብዙም ሳይቆይ በምእራባዊ ክፍለ አለም በሰዎች መካከል የሰጠው የኢየሱስ ክርስቶስ የግል አገልግሎት ታሪክ ይገኙበታል። ይህም የሕይወትን ዓላማ ያስተምራል እንዲሁም ለዚያ ዓላማ መሠረታዊ የሆነውን የክርስቶስን ትምህርት ያብራራል፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ተጓዳኝ ቅዱስ ቃል፣ መፅሀፈ ሞርሞን የሰው ልጆች በሙሉ የሰማይ አፍቃሪ አባት ወንድ ልጆች እና ሴት ልጆች እንደሆኑ፣ እርሱ ለህይወታችን መለኮታዊ እቅድ እንዳለው እና ልጁ ኢየሱስ ክርስቶስም ዛሬ እንደ ጥንቶቹ ቀናት እንደሚናገር ይመሰክራል።

እኛ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ሚያዚያ 6 ቀን 1830(እ.ኤ.አ) ዓ.ም እንደተመሰረተች እና የተመለሰችው የክርስቶስ የአዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን እንደሆነች እናውጃለን፡፡ ይህች ቤተክርስቲያን በዋነኛው የማዕዘን ራስዋ ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጹም ህይወት እና መጨረሻ በሌለው የኃጢያት ክፍያው እና በእውኑ ትንሳኤው ላይ ተተክላለች። ኢየሱስ ክርስቶስ እንደገና ሐዋርያትን ጠርቶ የክህነት ስልጣን ሰቷቸዋል። መንፈስ ቅዱስን፣ የደህንነትን ስነስርዓቶችን ለመቀበል እና ዘላቂ ደስታን ለማግኘት ሁላችንም ወደ እርሱ እና ወደ ቤተክርስቲያኑ እንድንመጣ ይጋብዘናል።

“ይህ ተሃድሶ በእግዚአብሔር አብ እና በተወዳጅ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ከተጀመረ ሁለት መቶ ዓመታት አልፈዋል። በዓለም ዙሪያ ያሉ በሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች እነዚህን የተተነበዩ ክስተቶች እውቀት ተቀብለዋል።

“ቃል የተገባለት መልሶ መቋቋም በቀጣይ መገለጥ ወደፊት እንደሚሄድ በደስታ እናውጃለን። እግዚአብሄር “ሁሉንም በክርስቶስ አንድ ላይ ስለሚጠቀልል” ምድር እንደገና ተመሳሳይ አትሆንም።

“በአክብሮትና በአመስጋኝነት፣ እኛ እንደ እርሱ ሐዋሪያት ሰማያት ክፍት መሆናቸውን እንደምናውቅ ሁላችሁም እንድታውቁ እንጋብዛለን። እግዚአብሔር ለሚወዳቸው ወንዶችና ሴቶች ልጆቹ ፈቃዱን እያሳየ መሆኑን እናረጋግጣለን። የዳግም መመለስ መልዕክትን በጸሎት የሚያጠኑ እና በእምነት የሚተገብሩ ሰዎች ስለመለኮታዊነቱ እና ለአለም ተስፋ ለተገባው ለጌታችን እና ለአዳኛችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም ምፅዓት ለማዘጋጀት ስላለው እቅድ የራሳቸውን ምስክርነት በማግኘት እንደሚባረኩ እንመሰክራለን።15

የተወደዳችሁ ወንድሞች እና እህቶች፣ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል በሙላት በዳግም መመለሷን በተመለከተ ለዓለም ሁሉ የተነገረው የሁለት ምእተ አመታት መታሰቢያ አዋጅ ይህ ነው። በ 12 ቋንቋዎች ተተርጉሟል። ሌሎች ቋንቋዎች በቅርቡ ይከተላሉ፡፡ ቅጂውን እንዲያገኙ በቤተክርስቲያኑ ድህረ ገጽ ላይ ወዲያውኑ ይለቀቃል። በግል እና ከቤተሰብዎ አባላት እና ጓደኞች ጋር ያጥኑት፡፡ እውነቶቹን አሰላስሉ እና እነዛ እውነቶች በህይወትዎ ላይ ምን ያህል ተጽዕኖ እንደሚኖራቸው አስቡበት፣ እነሱን አድምጡ፣ እና አብረው የሚጓዙትን ትእዛዛት እና ቃል ኪዳኖች ተከተሉ።

ዮሴፍ ስሚዝ ጌታ የመጨረሻውን የዘመን ፍጻሜ ለመክፈት አስቀድሞ የመረጠው ነቢይ እንደሆነ አውቃለሁ። በእርሱም በኩል፣ የጌታ ቤተክርስቲያን በምድር ላይ በዳግም ተመልሳለች። ጆሴፍም የእርሱን ምስክርነት በደሙ አትሟል። እንዴት ነው እርሱን የማፈቅረው እና የማከብረው!

እግዚአብሔር ህያው ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ነው! የእርሱ በተክርስቲያን በዳግም ተመልሳለች! እርሱ እና አብ፣ የሰማይ አባታችን፣ እኛን እየተመለከቱ ናቸው። ይህንን የምመሰክረው ቅዱስ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው፣ አሜን።

አትም