አጠቃላይ ጉባኤ
በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ አተኩሩ
የሚያዝያ 2023 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ አተኩሩ

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ለችግሮቻችን መፍትሄ ነው፣ ነገር ግን እርሱን ለማየት ዓይኖቻችንን በማንሳት እይታችንን እሱ ላይ ማድረግ አለብን።

አባቴ “መፍትሄን ማየት እስከማትችል ድረስ በችግሮችህ ላይ በሃይል አታተኩር” ይለኝ ነበር።

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በጣም አስቸጋሪ ለሆኑ ችግሮቻችን እንኳን መፍትሄ እንደሆነ እመሰክራለሁ። በተለይም እያንዳንዳችን የሚያጋጥሙንን እና ማንኛችንም በራሳችን ልንፈታው የማንችላቸውን አራት ችግሮች አሸንፏል።

  1. የመጀመሪያው ችግር አካላዊ ሞት ነው። እሱን ለማዘግየት ወይም ችላ ለማለት መሞከር እንችላለን ነገር ግን በራሳችን ማሸነፍ አንችልም። ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ለእኛ ሞትን አሸንፏል፣ እናም በዚህ ምክንያት ሁላችንም አንድ ቀን ትንሳኤ እናደርጋለን። 1

  2. ሁለተኛው ችግር የዚህን ዓለም መከራዎች፣ አስቸጋሪ ገጠመኞች፣ ሀዘን፣ ህመም እና ኢፍትሃዊነት ያጠቃልላል። ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ሁሉ አሸንፏል። እሱን ለመከተል ለሚጥሩ፣ አንድ ቀን “እንባዎችን ሁሉ ያብሳል” እና ነገሮችን እንደገና ያስተካክላል። 2 እስከዚያው ድረስ፣ ፈተናዎቻችንን በልበ ሙሉነት፣ በደስታ እና በሰላም እንድናልፍ ያበረታናል።3

  3. ሦስተኛው ችግር በኃጢአት ምክንያት የሚመጣ መንፈሳዊ ሞት ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ “የሰላማችንን ተግሣጽ” በራሱ ላይ በመውሰድ ይህን ችግር አሸንፏል።4 በእሱ የሃጢያት ክፍያ መስዋዕት ምክንያት፣ በአዳኙ ላይ እምነት ካለን፣ በቅንነት ንስሀ ከገባን፣ አብ የሚሰጠንን ቃል ኪዳን እንደ ጥምቀት ባሉ አስፈላጊ ሥርዓቶች ከተቀበልን እና እስከ መጨረሻው ከጸናን ከኃጢአታችን መዘዝ ነፃ ልንወጣ እንችላለን።5

  4. አራተኛው ችግር ውስን የሆነው ፍጽምና የጎደለው ተፈጥሮአችን ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ ለዚህም ችግር መፍትሔ አለው። እሱ ስህተቶቻችንን እንዲሁ ሰርዞ እንደገና ንጹህ ብቻ አይደለም የሚያደርገን። እርሱ “ያለማቋረጥ መልካምን መስራት እንጂ ከእንግዲህ ሃጥያት ለመፈጸም ምንም ፍላጎት እንዳይኖረን ታላቅ ለውጥ በልባችን ውስጥ” ሊያደርግ ይችላል። 6 በክርስቶስ ጸጋ ፍጹማን ልንሆን እና አንድ ቀን እርሱን ልንመስል እንችላለን። 7

እንደ አለመታደል ሆኖ፣ ብዙ ጊዜ በራሳችን ችግሮች ላይ በማተኮር መፍትሄ በሆነው በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለንን ትኩረት እናጣለን። ያንን ስህተት እንዴት ነው ማስወገድ የምንችለው? መልሱ ከእሱ እና ከሰማይ አባታችን ጋር እንድንገባ በተጋበዝነው ቃል ኪዳኖች ውስጥ እንዳለ አምናለሁ።

በቃል ኪዳኖች በኩል በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ማተኮር

ቃል ኪዳኖቻችን ትኩረታችንን፣ ሀሳባችንን እና ተግባራችንን በክርስቶስ ላይ እንድናተኩር ይረዱናል። “[ከገባናቸው] ቃል ኪዳኖች ጋር ስንጣበቅ፣ “የዚህን ዓለም ነገሮች” “ወደ ጎን [ለመተው]” እና “የተሻለውን [ዓለም] ነገር” በትጋት ልንፈልግ እንችላለን።8

በመፅሐፈ ሞርሞን ውስጥ የአሞን ሰዎች ያደረጉት ይህንኑ ነው። ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲማሩ እና ሕይወታቸውን በእርሱ ላይ ማተኮር ሲጀምሩ፣ የጦር መሣሪያዎቻቸውን መቅበር እንዳለባቸው ተገንዝበው ፍጹም ሐቀኛ እና “ለእግዚአብሔር ባላቸው ቅንዓት የተለዩ” ሆኑ። 9

ቃል ኪዳኑን ማክበር የመንፈስን ተፅእኖ የሚጋብዝ ማንኛውንም ነገር እንድንፈልግ እና የሚያባርረውን ሁሉ ደግሞ ወደመተው ይመራናል—“ለመንፈስ ቅዱስ መገኘት ብቁ መሆን ከቻልን በሰማይ አባት እና በልጁ ኢየሱስ ክርስቶስ ፊት ለመኖር ብቁ እንድንሆን እናውቃለንና።10 ይህ ማለት መልካም ቃላትን በመጠቀም ቃላቶቻችንን መለወጥ አለብን ማለት ሊሆን ይችላል። ይህ ማለት በመንፈሳዊ ጤናማ ያልሆኑ ልማዶችን ከጌታ ጋር ያለንን ግንኙነት በሚያጠናክሩ አዳዲስ ልማዶች መተካት ማለት ሊሆን ይችላል።

ፕሬዚዳንት ራስል ኤም. ኔልሰን “በጥምቀት ገንዳ ውስጥ እና በቤተመቅደስ ውስጥ ቃል ኪዳን የሚገባ—እና የሚያከብር—እያንዳንዱ ሰው የኢየሱስ ክርስቶስን ሀይል ለማግኘት ተጨማሪ ችሎታ እንዳለው ተናግረዋል።…

“ቃል ኪዳኖችን የመጠበቅ ሽልማት የሰማይ ሀይል ነው—ያም ሀይል መከራዎቻችንን፣ ፈተናዎቻችንን እና ከባድ ሀዘኖቻችንን በተሻለ ሁኔታ እንድንቋቋም ያጠነክረናል” በማለት ተናግረዋል።11

በእያንዳንዱ እሁድ በሚደረገው ቅዱስ ቁርባን ላይ ቃል ኪዳኖቻችንን ማደሳችን እራሳችንን የመመርመር እና ህይወታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የማተኮር ትልቅ እድል ነው።12 ቅዱስ ቁርባንን በመካፈል፣ “ሁልጊዜ እሱን [እንደምናስታውሰው]” እናውጃለን። 13 ሁልጊዜ የሚለው ቃል በጣም አስፈላጊ ነው። የአዳኙን ተጽእኖ በሁሉም የህይወታችን ክፍል ያዳርሳል። እርሱን በቤተክርስቲያን ውስጥ ወይም በጠዋት ጸሎታችን ወይም በችግር ውስጥ ስንሆን ብቻ እና አንድ ነገር ሲያስፈልገን ብቻ አናስታውሰውም።

አዎን፣ አንዳንድ ጊዜ ትኩረታችን በሌላ ነገር ይወሰዳል። እንረሳለን። ትኩረታችንን እናጣለን። ነገር ግን ቃል ኪዳኖቻችንን ማደስ ማለት አዳኙን ሁል ጊዜ ለማስታወስ መፈለግ፣ ሳምንቱን በሙሉ ይህን ለማድረግ መሞከር እና በሚቀጥለው ሳምንት በቅዱስ ቁርባን ጠረጴዛ ላይ እንደገና በእሱ ላይ እናተኩራለን ማለት ነው።

በቤታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ማተኮር

በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ማተኮር እሁድ በቤተክርስቲያን ውስጥ ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ያለፈ መሆን አለበት። ፕሬዚዳንት ኔልሰን በ2018 ኑ፣ ተከተሉኝን ሲያስተዋውቁ፣ “ጊዜው ቤትን ያማከለ ቤተክርስቲያን ነው በማለት ተናግረዋል።14 “ቤታችንን ወደ እምነት መቅደስ” እና “የወንጌል ትምህርት ማዕከል አድርገን መለወጥ አለብን” ብለዋል። እንዲህ የምናደርግ ከሆነ አራት አስደናቂ ተስፋዎችን ሰጥቶናል።15

የመጀመሪያው ተስፋ፡- “የሰንበት ቀናችሁ በእውነት አስደሳች ይሆናሉ። ወደ አዳኛችን የምንቀርብበት ቀን ይሆናል። አንዲት የፔሩ ወጣት ሴት እንደተናገረችው፣ “የጌታ ቀን ከጌታ ብዙ መልስ [የማገኝበት] ቀን ነው።”

ሁለተኛው ተስፋ፡የእናንተ ልጆች የአዳኙን ትምህርቶች ለመማር እና በእነዚህም በመኖር ይደሰታሉ።” በዚህ ምክንያትም “ስለ ክርስቶስ እንናገራለን፣ እኛ በክርስቶስ እንደሰታለን፣ እናም ስለ ክርስቶስ እንሰብካለን… ልጆቻችን የኃጢያታቸውን ስርየት ከየት እንደሚፈልጉ ያውቁ ዘንድ ፡፡” 16

ይህን የምናደርገው አንድ ቀን፣ ልጃችን ሄኖስ እንዳደረገው ለሥራ ወይም በተራራ ላይ በእግር ለመጓዝ ወይም በጫካ ውስጥ አውሬ ለማደን ሲወጣ ስለ ክርስቶስ ያስተማርነውን በወንጌል መኖር የሚያስገኘውን ደስታ እንዲያስታውስ ነው። . እና ማን ያውቃል? “ኃጢአትህ ይቅር ተብሎልሃል እና አንተ ትባረካለህ” የሚለውን የጌታን ድምፅ መስማት ይችል ዘንድ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያዞረው መንፈሳዊ ረሃብ በመጨረሻ የሚሰማበት ቀን ይህ ሊሆን ይችላል።17

ሦስተኛው የተስፋ ቃል “ጠላት በእናንተ ህይወት እና በእናንተ ቤት ውስጥ ያለው ተፅዕኖ ይቀንሳል” ለምን? ምክንያቱም በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ባተኮርን ቁጥር ኃጢያት የመማረክ ሃይሉን ያጣል። 18 ቤቶቻችን በአዳኙ ብርሃን እየተሞሉ ሲሄዱ፣ ለጠላት ጨለማ ቦታ እየቀነሰ ይሄዳል።

አራተኛው የተስፋ ቃል፦ “በቤተሰባችሁ ውስጥ ያለው ለውጥ ታላቅ እና የሚቀጥል ይሆናል።” ለምን? ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያመጣው ለውጥ “ታላቅ ለውጥ” ስለሆነ ነው።19 እርሱ የእኛን ተፈጥሮ ይለውጣል፣ “አዲስ ፍጥረታት” እንሆናለን።20 እኛ ለሁሉም የእግዚአብሔር ልጆች ባለው ንጹህ ፍቅር ተሞልተን ቀስ በቀስ እንደ አዳኙ እንሆናለን።

እነዚህ ተስፋዎች በህይወታቸው እና በቤተሰባቸው ውስጥ እንዲፈጸሙ የማይፈልግ ማን ነው? እነሱን ለማግኘት ምን ማድረግ ያስፈልገናል? መልሱ ቤታችንን ወደ የእምነት መቅደስ እና የወንጌል ትምህርት ማዕከል መለወጥ ነው። እና ደግሞ ያንን እንዴት ነው ማድረግ የምንችለው? በቤታችን ውስጥ በጣም አስፈላጊው ተጽእኖ በሆኑት የሰማይ አባት እና ኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በማተኮር፣ እነሱን የቤተሰብ ህይወታችን ማእከል በማድረግ ነው።

በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ የሚገኙትን የክርስቶስን ቃላት የሕይወታችሁ የዕለት ተዕለት ክፍል በማድረግ እንድትጀምሩ ልጠቁም? ለቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት ፍጹም የሆነ የተደነገገ ቀመር የለም። በየቀኑ 5 ወይም 10 ደቂቃ ሊሆን ይችላል - ወይም ከቻላችሁ የበለጠ። በቀን አንድ ምዕራፍ ወይም ጥቂት ቁጥሮች ሊሆን ይችላል። አንዳንድ ቤተሰቦች ወደ ትምህርት ቤት ወይም ሥራ ከመሄዳቸው በፊት በማለዳ ማጥናት ይመርጣሉ። ሌሎች ደግሞ ከመተኛታቸው በፊት በማታ ማንበብ ይመርጣሉ። አንዳንድ ወጣት ባለትዳሮች ወደ ሥራ በሚሄዱበት ጊዜ ለየብቻቸው እንደሚያጠኑና ከዚያም ግንዛቤያቸው እና ውይይታቸው እንዲቀዳ በጽሁፍ መልዕክት እንደሚያካፍሉ ነግረውኛል፤ በዚህም አስተያየታቸውና ውይይታቸው ይመዘገባል።

ኑ፣ ተከተሉኝ ለግለሰቦች እና ለቤተሰቦች የወንጌል መርሆችን ከቅዱሳት መጻህፍት እንዲማሩ የሚያግዙ ብዙ የተግባር ሃሳቦችን እና ግብዓቶችን ያቀርባል። የመጽሐፍ ቅዱስ እና የመጽሐፈ ሞርሞን ቪዲዮዎች ቅዱሳት መጻሕፍትን ለቤተሰባችሁ ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ጠቃሚ መሣሪያዎች ሊሆኑ ይችላሉ። ብዙ ጊዜ ታዳጊዎች እና ልጆች በቅዱሳት መጻህፍት ውስጥ ባሉ የማይረሱ ታሪኮች ይነሳሳሉ። እነዚህ ታሪኮች እና የሚያስተምሯቸው የወንጌል መርሆች ልክ እንደ ታማኝ ጓደኞች፣ ጥሩ የአገልግሎት፣ በጎነት፣ ታዛዥነት፣ ትዕግስት፣ ጽናት፣ የግል መገለጥ፣ ልግስና፣ ትህትና እና በኢየሱስ ክርስቶስ እምነት ምሳሌ ሲፈልጉ ከልጆቻችሁ ጋር ይቆያሉ። በጊዜ ሂደት የእናንተ የእግዚአብሔርን ቃል በመመገብ ወጥነታችሁ ልጆቻችሁ ወደ አዳኙ እንዲቀርቡ ይረዳቸዋል። ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ያውቁታል።

ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዛሬ ህያው ነው። እሱ በህይወታችን ውስጥ ንቁ፣ የእለት ተእለት መገኘት ሊሆን ይችላል። እርሱ ለችግሮቻችን መፍትሄ ነው፣ ነገር ግን እርሱን ለማየት ዓይኖቻችንን በማንሳት እይታችንን እሱ ላይ ማድረግ አለብን። “ባሰባችሁት ነገር ሁሉ ወደ እኔ ተመልከቱ፣ አትጠራጠሩ፣ አትፍሩ፡” 21 በማለት ተናግሯል። በእርሱ እና በሰማዩ አባታችን ላይ ስናተኩር፣ ከነሱ ጋር ቃል ኪዳኖችን ስንገባ እና ስንጠብቃቸው እና በቤታችን እና በቤተሰባችን ውስጥ በጣም አስፈላጊ ተፅእኖዎች ስናደርጋቸው፣ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ያሰቡት አይነት ሰዎች እንሆናለን፡-”ጌታ ዳግም በሚመጣበት ጊዜ ለመቀበል የሚችል፣ ዝግጁ እና ብቁ የሆነ ፣ በዚህ በወደቀው አለም ላይ ኢየሱስ ክርስቶስን የመረጠ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ የላቀ እና ቅዱሳን ህጎችን ለመኖር በተሰጠው ስልጣን የሚደሰት ህዝብ።” 22 በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።

አትም