አጠቃላይ ጉባኤ
በክርስቶስ አንድነት
የሚያዝያ 2023 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


በክርስቶስ አንድነት

አንድ ለመሆን ተስፋ ማድረግ የምንችለው ለኢየሱስ ክርስቶስ ባለን በግለሰብ ታማኝነት እና ፍቅር ብቻ ነው።

ፕሬዘደንት ዳለን ኤች. ኦክስ እንዳጠቆሙት፣ ዛሬ የሆሳእና በዓል ነው፤ ይህም ጌታ ወደ ኢየሩሳሌም በድል አድራጊነት የገባበትን፣ ከቀናት በኋላ በጌቴሴማኒ የተሰቃየበትን እና በመስቀል ላይ መሞቱን፣ እና በፋሲካ እሁድ የከበረ ትንሳኤውን የሚያመለክተውን የቅዱስ ሳምንት መጀመሪያ ነው። ክርስቶስ ለእኛ ዋጋ ለመክፈል የተቀበለውን ነገር ፈጽሞ ላለመርሳት እንወስን።1 በመቃብር ላይ ያለውን የእርሱን ድል እና ሁለንተናዊ የትንሣኤ ስጦታን ስናሰላስል በፋሲካ እንደገና የሚሰማንን ታላቅ ደስታ መቼም አንጣ።

እርሱን ከጠበቁት ፈተናዎች እና ስቅለት በፊት በነበረው ምሽት፣ ኢየሱስ ከሐዋርያቱ ጋር ለፋሲካ እራት ተቀላቀለ። በዚህ የመጨረሻ እራት ማብቂያ ላይ፣ በተቀደሰ የምልጃ ጸሎት፣ ኢየሱስ አባቱን እንዲህ ሲል ተማጽኗል፦ “ቅዱስ አባት ሆይ፥ እነዚህን የሰጠኸኝን [የእኔን ሐዋርያት] እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው።”2

ከዚያም፣ በትህትና፣ አዳኙ ሁሉንም አማኞች ለማካተት አቤቱታውን አሰፋ፡–

“ከቃላቸው የተነሳ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ አልለምንም፤

“እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፣ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ።”3

አንድ መሆን በኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ውስጥ እና እግዚአብሔር ከልጆቹ ጋር ባለው ግንኙነት የሚደጋገም ጭብጥ ነው። በሄኖክ ጊዜ ውስጥ ያለችውን የጽዮን ከተማ አስመልክቶ፣ “እነርሱ አንድ ልብ እና አንድ አእምሮ ነበሩ” ተብሎ ተነግሯል።4 በጥንታዊው የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ከቀደሙት ቅዱሳን የአዲስ ኪዳን መዝገቦች፣ “ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሯቸው።”5

በእኛ ዘመን፣ ጌታ እንዲህ መክሯል፤ “እንዲህ እላችኋለሁ፣ አንድ ሁኑ፤ እናም አንድ ካልሆናችሁ የእኔ አይደላችሁም።”6 በምዙሪ የነበሩት የጥንት ቅዱሳን የጽዮንን ቦታ መመስረት ያልቻሉበትን ምክንያት ጌታ ከተናገረባቸው ምክንያቶች መካከል “በሰለስቲያል መንግስት ህግ መሰረት አስፈላጊ በሆነው ህብረትም አይተባበሩም።”7

እግዚአብሔር በሁሉም ልቦች እና አእምሮዎች ውስጥ በሚያሸንፍበት፣ ህዝቡ “በአንድ የክርስቶስ ልጆች” ተብለው ተገልጸዋል።8

ከሞት የተነሳው አዳኝ ለጥንታዊው የመፅሐፈ ሞርሞን ህዝቦች ሲገለጥ፣ በቀደመው ጊዜ በጥምቀት እና በሌሎች ጉዳዮች ላይ በሰዎች መካከል አለመግባባቶች እንደነበሩ በመቃወም ገልጿል። እርሱም እንዲህ አዘዘ፦

“ከዚህ በፊት እንደነበረውም በመካከላችሁ ፀብ አይኖርም፤ ከዚህ በፊት እንደነበረው በትምህርቴ ነጥቦችም ምክንያት በመካከላችሁ ፀብ አይኖርም።

“እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ የፀብ መንፈስ ያለበት፣ የፀብ አባት ከሆነ እናም የሰዎችን ልብ እርስ በርስ እንዲጣሉ በቁጣ ከሚያነሳሳው ከዲያብሎስ እንጂ፤ ከእኔ አይደለም።”9

በእኛ ፀብ በሞላበት አለም፣ እንዴት ነው አንድነት ሊገኝ የሚችለው፣ በተለይም “አንድ ጌታ፣ አንድ ሃይማኖት፣ አንዲት ጥምቀት” በሚኖረን ቤተክርስቲያን ውስጥ?10 ጳውሎስ ቁልፉን ይሰጠናል፦

“ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁሉ ክርስቶስን ለብሳችኋልና።

“አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና።”11

እኛ በጣም የተለያየን ነን እና በማንኛዉም መሰረት ወይም በሌላ ስም አንድ ላይ ለመሰባሰብ አንዳንዴም በጣም ተቃራኒዎች ነን። በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ በእውነት አንድ መሆን እንችላለን።

በክርስቶስ አንድ መሆን ከግል ይጀምራል—እኛ እያንዳንዳችን ከራሳችን እንጀምራለን። የሥጋና የመንፈስ መንታ ፍጡራን ነን እናም አንዳንዴ ከራሳችን ጋር ጦርነት ውስጥ እንገባለን። ጳውሎስ እንደገለፀው፦

“በውስጡ ሰውነቴ በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለኛልና፤

“ነገር ግን በብልቶቼ ከአእምሮዬ ሕግ ጋር የሚዋጋውንና በብልቶቼ ባለ በኃጢአት ሕግ የሚማርከኝን ሌላ ሕግ አያለሁ።”12

ኢየሱስ ክርስቶስም የስጋና አጥንት ሰውነት ነበርው። እርሱ ተፈትኖ ነበር፤ ይረዳል፤ በውስጣችን አንድነትን እንድናሳካ ሊረዳን ይችላል።13 ስለዚህ፣ በክርስቶስ ብርሃን እና ጸጋ በመሳብ፣ መንፈሳችንን እና መንፈስ ቅዱስን በሥጋዊው ላይ የበላይነትን ለመስጠት እንጥራለን። ስንስት፣ ክርስቶስ በኃጢያት ክፍያው፣ የንስሐን ስጦታ እና እንደገና እንድንሞክር እድል ሰጥቶናል።

በግለሰብ ደረጃ “ክርስቶስን ከለበስን” ጳውሎስ እንደተናገረው አንድ ላይ ሆነን “የክርስቶስን አካል” እንደምንሆን ተስፋ እናደርጋለን።14 “ክርስቶስን መልበስ” በእርግጥም “ፊተኛይቱ እና ታላቂቱ ትእዛዛቱን” 15 የመጀመሪያችን እና ታላቅ ቁርጠኝነታችንን ይጨምራል፣ እናም እግዚአብሔርን ከወደድን፣ ትእዛዛቱን እንጠብቃለን። 16

በክርስቶስ አካል ውስጥ ካሉ ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ጋር አንድነት የሚያድገው ከመጀመሪያው ጋር በማይነጣጠል መልኩ የተገናኘውን ሌሎችን እንደ ራሳችን እንድንወድ የሚያቀርበውን ሁለተኛውን ትእዛዝ ስንከተል—ነው።17 እንዲሁም የአዳኙን ከፍተኛ እና ቅዱስ የሆነውን የዚህን ሁለተኛ ትእዛዝ፣ እንዲሁም እራሳችንን እንደ መውደድ ብቻ ሳይሆን እርሱ እንደወደደን እርስ በርሳችን የምንዋደድበትን አገላለጽ፣ ከተከተልን የበለጠ ፍጹም አንድነት በመካከላችን እንደሚገኝ አስባለሁ18 በአጠቃላይ፣ “እያንዳንዱ ሰው የባልንጀራውን ፍላጎት እንዲሻ፣ እናም ለሁሉም ነገሮች ሙሉ አይኑን ወደ እግዚአብሔር ክብር ያደርግ ዘንድ ነው።”19

ፕሬዘዳንት ሜሪየን ጂ. ሮምኒ፣ የቀዳሚ አመራር የቀድሞ አማካሪ፣ ዘላቂ ሰላም እና አንድነት እንዴት እንደሚገኝ ሲያብራሩ፣ እንዲህ ብለዋል፦

“አንድ ሰው፣ ለሰይጣን የሚገዛ የሥጋ ሥራ ቢሞላው፣ በእራሱ ውስጡ ይዋጋል። ሁለት ሰዎች ቢገዙ፣ እያንዳንዳቸው በውስጣቸው ይዋጋሉ እና እርስ በራስ ይጣላሉ። ብዙ ሰዎች ቢገዙ፣ አንድ ማህበረሰብ ከፍተኛ ጭንቀት እና ጠብ ያጭዳል። የአገር መሪዎች ቢገዙ፣ የአለም–አቀፍ ጠብ ይኖራል።”

ፕሬዘደንት ሮምኒ እንዲህ በማለት ቀጠሉ፣ “የሥጋ ሥራ ዓለም አቀፋዊ እንደሆነ፣ የሰላም ወንጌልም እንዲሁ ነው። አንድ ሰው የሚኖረው ከሆነ፣ በራሱ ውስጥ ሰላም አለው። ሁለት ሰዎች ቢኖሩት፣ እያንዳንዳቸው በውስጣቸው እና እርስ በራስ ሰላም ይኖራቸዋል። ዜጎች ቢኖሩት፣ አገር በውስጧ ሰላም ይኖራታል። የዓለም ጉዳዮችን ለመቆጣጠር በመንፈስ ፍሬ የሚደሰቱ በቂ ብሔራት ሲኖሩ፣ ያኔ፣ እና ያኔ ብቻ፣ የጦርነት ከበሮ አይመታም፣ እናም የውጊያው ባንዲራዎች ይታሰራሉ። (አልፍሬድ ሎርድ ቴኒሰን, “Locksley Hall,” The Complete Poetical Works of Tennyson, ed. ደብልዩ. ጄ. ሮልፍ, Boston: Houghton-Mifflin Co., 1898, p. 93, lines 27–28.ይመልከቱ)”20

እኛ “ክርስቶስን [ስንለብስ]”፣ ልዩነቶችን፣ አለመግባባቶችን እና ጥሎችን መፍታት ወይም ወደ ጎን መተው ይቻላል። መከፋፈልን የማሸነፍ አስደናቂ ምሳሌ በቤተክርስቲያናችን ታሪክ ውስጥ ይገኛል። በ1857 በእንግሊዝ ውስጥ የተወለዱት ሽማግሌ ብሪገም ሄንሪ ሮበርትስ (በተለምዶ ቢ. ኤች. ሮበርትስ ተብለው የሚታወቁት)፣ እኛ ዛሬ የሰባው ፕሬዘደንት ብለን የምንጠራው ፣ የሰባዎቹ የመጀመሪያ ሸንጎ አባል ሆነው አገልግለዋል። ሽማግሌ ሮበርትስ በዳግም ለተመለሰው ወንጌል እና ለቤተክርስቲያኗ በአንዳንድ በጣም አስቸጋሪ ጊዜዎች ችሎታ ያላቸው እና የማይታክቱ ጠበቃ ነበሩ።

ምስል
ወጣቱ ቢ. ኤች. ሮበርትስ

ሆኖም፣ በ1895 (እ.አ.አ)፣ የሽማግሌ ሮበርትስ በቤተክርስቲያኗ ውስጥ የነበራቸው አገልግሎት በጠብ ምክንያት አደጋ ላይ ወድቆ ነበር። ቢ። ኤች. የዩታ ህገ መንግስት ባዘጋጀው የአውራጃ ስብሰባ ተወካይ ሆነው ተሹመው ነበር። በዚያ አመት ለዩናይትድ ስቴትስ ኮንግረስ እጩ ሆኑ፣ ነገር ግን ለቀዳሚ አመራር አላሳወቁም ወይም ፍቃድ አልጠየቁም ነበር። ፕሬዘደንት ጆሴፍ ኤፍ. ስሚዝ፣ የቀዳሚ አመራር አማካርሪ፣ ቢ. ኤች. ለነበረው ለዚያ ውድቀት በአጠቃላይ የክህነት ስብሰባ ላይ ወቅሰውት ነበር። ሽማግሌ ሮበርትስ በምርጫው ተሸነፉ እና ሽንፈቱ በፕሬዘደንት ስሚዝ መግለጫዎች ምክንያት እንደሆነ ተሰምቷቸው ነበር። በአንዳንድ የፖለቲካ ንግግሮች እና ቃለመጠይቆች የቤተክርስቲያኗን መሪዎች ተቹ። ከቤተክርስቲያኗ አገልግሎት ርቀውም ሄዱ። በሶልት ሌክ ቤተመቅደስ ውስጥ ከመጀመሪያ አመራር አባላት እና ከአስራ ሁለቱ ሸንጎ አባላት ጋር ከሚደረገው ረጅም ስብሰባ፣ ቢ. ኤች. እራሳቸውን በመከላከል ጸኑ። በኋላም፣ “ፕሬዘደንት [ዊልፎርድ] ዉድሩፍ ለ[ሽማግሌ ሮበርትስ] ደግመው እንዲያስቡበት ሶስት ሳምንት ሰጧቸው። ንሰሃ ሳይገቡ ከቀጠሉ፣ ከሰባው ጉባኤ ሊሰናበቱ ነበር።”21

ከሐዋሪያት ሒበር ጄ.ግራንት እና ፍራንሲስ ሊማን ጋር በተደረገው ቀጣይ የግል ስብሰባ፣ ቢ. ኤች. መጀመሪያ ለመቀየር የማይፈልጉ ነበር፣ ነገር ግን ፍቅር እና መንፈስ ቅዱስ አሸነፉ። እምባ ወደ አይናቸው መጣ። ሁለቱ ሐዋርያት ቢ. ኤችን አስቸግረዋቸው የነበሩትን ጥቃቶችን እና አስጨናቂ ጥፋቶች ምላሽ መስጠት ቻሉ። እና እርቅ እንዲደረግ ከልብ በመማጸን ሄዱ። በቀጣዩ ጠዋት፣ ከረ፤ጅም ፀሎት በኋላ፣ ሽማግሌ ሮበርትስ ከወንድሞቻቸው ጋር ዳግም ለመገናኘት መዘጋጀታቸውን ለሽማግሌ ግራንት እና ላይማን በጽሁፍ ላኩ።22

በኋላ ከቀዳሚ አመራር ጋር በተገናኙ ጊዜ፣ ሽማግሌ ሮበርትስ እንዲህ አሉ፣ “ወደ ጌታ ሄጄ ለእግዚአብሔር ስልጣን ለመገዛት በመንፈሱ በኩል ብርሃን እና መመሪያ ተቀበልኩ።”23 ለእግዚአብሔር ባላቸው ፍቅር ተነሳስተው፣ ቢ. ኤች. ሮበርትስ ታማኝ እና ብቁ የቤተክርስቲያኗ መሪ በመሆን እስከ ህይወታቸው ፍፃሜ ድረስ ቆይተዋል።24

ምስል
ሽማግሌ ቢ. ኤች. ሮበርትስ

በዚህ ምሳሌ ላይም አንድነት ማለት ሁሉም ሰው “የራሱን ወይም የራሷን ነገር ማድረግ” እንዳለበት ወይም በራሱ ወይም በራሷ መንገድ ለመሄድ መስማማት ብቻ እንዳልሆነ ማየት እንችላለን። ሁላችንም ጥረታችንን ለጋራ ዓላማ ካላጣመርን አንድ መሆን አንችልም። ያ ማለት፣ በቢ. ኤች. ሮበርትስ ቃላት፣ ለእግዚአብሔር ስልጣን መገዛት ማለት ነው። እኛ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ተግባራትን የምንፈጽም የተለያዩ የክርስቶስ አካል ብልቶች ነን፣—ጆሮ፣ ዓይን፣ ራስ፣ እጅ፣ እግር—ግን ሁሉም የአንድ አካል ናቸው።25 ስለዚህ፣ ግባችን “ነገር ግን ብልቶች እርስ በርሳቸው በትክክል ይተሳሰቡ ዘንድ እንጂ በአካል መለያየት እንዳይሆን ነው።”26

አንድነት መመሳሰልን አይጠይቅም፣ ግን መስማማትን ይጠይቃል። ልባችንን በፍቅር ማስተሳሰር፣ በእምነት እና አስተምህሮ አንድ መሆን፣ እና አሁንም ለተለያዩ ቡድኖች መደሰት፣ በተለያዩ የፖለቲካ ጉዳዮች ላይ አለመስማማት፣ በግቦች እና በትክክለኛው መንገድ መከራከር፣ እና ሌሎችም ብዙ ነገሮችን ማድረግ እንችላለን። ነገር ግን በፍፁም አለመስማማት ወይም በቁጣ ወይም እርስ በርስ በመናቅ ልንከራከር በምንም አንችልም። አዳኙ እንዲህ ብሏል፦

“እውነት፣ እውነት እላችኋለሁ፣ የፀብ መንፈስ ያለበት፣ የፀብ አባት ከሆነ እናም የሰዎችን ልብ እርስ በርስ እንዲጣሉ በቁጣ ከሚያነሳሳው ከዲያብሎስ እንጂ፤ ከእኔ አይደለም።

“እነሆ፣ ሰዎችን አንዳቸውን ከሌላኛው ልባቸውን ለቁጣ የሚያነሳሳ ይህ የእኔ ትምህርት አይደለም፤ ነገር ግን እንደነዚህ ያሉ ነገሮች እንዲወገዱ ማድረግ ይህ የእኔ ትምህርት ነው።”27

ከአመት በፊት፣ ፕሬዘደንት ራስል ኤም. ኔልሰን በእነዚህ ቃላት እኛን ተማፀኑን፦ “ማንኛችንም ሃገራትን ወይንም የሌሎችን ድርጊቶች ወይንም የራሳችንን ቤተሰብ አባላት እንኳን መቆጣጠር አንችልም። ነገር ግን ራሳችንን መቆጣጠር እንችላለን። ውድ ወንድሞች እና እህቶች ዛሬ የማቀርብላችሁ ጥሪ በእናንተ ልብ በእናንተ ቤት እና በእናንተ ህይወት ውስጥ እየተነሱ ያሉትን ግጭቶች እንድታስወግዱ ነው። ያ ዝንባሌ ቁጣም ቢሆን፣ የሚወጋ አንደበት ወይም በጎዳችሁ ሰው ላይ የያዛችሁት ቂም ማንኛውንም እንዲሁም ሁሉንም ዝንባሌዎች ቅበሩ። አዳኙ ሌላኛውን ጉንጫችንንም እንድናዞር [3 ኔፊ 12፥39 ይመልከቱ] ጠላታችንን እንድንወድ እንዲሁም ለሚበድሉን እንድንጸልይ አዞናል[ 3 ኔፊ 12፥44]።”28

ደግሜ እላለሁ አንድ ለመሆን ተስፋ ሊኖረን የምንችለው ለኢየሱስ ክርስቶስ ባለን የግል ታማኝነት እና ፍቅር ብቻ ነው—ከራስ ጋር አንድ፣ በቤት አንድ ፣ በቤተክርስቲያን አንድ፣ ቀጥሎም በጽዮን አንድ፣ እና ከሁሉም በላይ፣ ከአብ እና ከወልድ እና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ ለመሆን።

ወደ ቅዱሱ ሳምንት ክንውኖቸ እና ወደ ቤዛችን የመጨረሻ ድል እመለሳለሁ። የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሳኤ ስለመለኮታዊነቱ እና ሁሉንም ነገር እንዳሸነፈ ይመሰክራል። ከእርሱ ጋር በቃል ኪዳን የታሰርን፣ እኛም ሁሉንም ነገር አሸንፈን አንድ እንደምንሆን ትንሳኤው ይመሰክራል። የእርሱ ትንሳኤ በእርሱ በኩል ህያውነት እና የዘለአለም ህይወት እውነታዎች መሆናቸውን ይመሰክራል።

በዚህ ጥዋት፣ ስለእውነተኛው ትንሳኤው እና ስለሚያመለክተው ሁሉ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እመሰክራለሁ፣ አሜን።

አትም