አጠቃላይ ጉባኤ
የቤተክርስቲያኗ ስም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም
የጥቅምት 2021 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ


የቤተክርስቲያኗ ስም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም

በሕያው ነብዩ አማካኝነት የተገለፀውን የጌታን ምክር በፍቃደኝነት ስንከተል በተለይም ከቀድሞ አስተሳሰባችን በተቃራኒው የሚሄድ ከሆነ፣ ትህትናን እና መስዋዕትነትን የሚጠይቅ ቢሆንም፣ ጌታ በተጨማሪ መንፈሳዊ ኃይል ይባርከናል።

ፕሬዚዳንት ረስል ኤም ኔልሰን ነሐሴ 16፣ 2018 (እ.አ.አ) በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ፦ “ጌታ ለቤተክርስቲያኑ ስለገለጠው የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን 1 ስለሚለው ስም አስፈላጊነት በአዕምሮዬ አሳይቶኛል ብለዋል። ራሳችንን ከእርሱ ፍላጎት ጋር የማስማማት ስራ በፊታችን አለብን።” 2

ከሁለት ቀናት በኋላ፣ በነሐሴ 18 በሞንትሪያል ካናዳ ውስጥ ከፕሬዚዳንት ኔልሰን ጋር ነበርኩኝ። በአስደናቂው ፓሌ ደ ኮንግሬ የተካሄደውን የአባል ስብሰባችንን ተከትሎ፣ ፕሬዚዳንት ኔልሰን ከዘጋቢዎች ለተነሱ ጥያቄዎችን መልስ ሰጡ። “[የቤተክርስቲያኗን ስም መመለስ እና] ከመቶ ዓመታት በላይ የነበረን ባህል መቀልበስ አስቸጋሪ እንደሚሆን” አሳወቁ። ነገር ግን “የቤተክርስቲያኗ ስም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም” ሲሉ አከሉ። 3

ከሰባት ሳምንታት በኋላ፣ ፕሬዚዳንት ኔልሰን በአጠቃላይ ጉባኤ ውስጥ እንዲህ ተናገሩ፦“ጌታ ለቤተክርስቲያኑ ስለወሰነው ስም አስፈላጊነት በአዕምሮዬ አሳይቶኛል፤ ይኸውም የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ነው። … አዳኙ እራሱ ነው፣ ‘ቤተክርስቲያኔ እንዲህ ተብላ ትጠራለች ያለው’”። ከዚያም ፕሬዚዳንት ኔልሰን፣ “የቤተክርስቲያኗ ስም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም” በማለት ደገሙ። 4

ጥሩ ጥያቄ

እንዲህ የሚል ጥሩ ጥያቄ ተነሳ፦ ለብዙ አስርተ ዓመታት “ሞርሞን” የሚለውን ቅፅል ስም ተቀብለን ሳለ “ለምን አሁን?” “የሞርሞን ታበርናክል መዘምራን፣” “እኔ ሞርሞን ነኝ” የሚለው የቪድዮ ሰፖት፣ “እኔ የሞርሞን ወንድ ልጅ ነኝ” የሚለው የህፃናት ምዝሙርስ?

የክርስቶስ ትምህርት የማይቀየር እና ዘላለማዊ ነው። ሆኖም፣ የአዳኙ ስራ የተለዩ እና አስፈላጊ እርምጃዎች የሚገለፁት በተገቢ ጊዚያቸው ነው። በዚህ ጥዋት ፕሬዚዳንት ኔልሰን እንዲህ ብለዋል፣ “ዳግም መመለሱ ሂደት ነው፤ በአንድ ጊዜ የሚሆን ክስተት አይደለም“ 5 ጌታ፣ “ሁሉም ነገሮች በጊዚያቸው ይከናወኑ ዘንድ ግድ ነው” ብሏል 6 የተገለጠውን የቤተክርስቲያኗን ስም በድጋሚ እያቋቋምነው ነው እናም ጊዚያችን አሁን ነው።

የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ምንነት እና እጣ ፈንታ በእርሱ ስም እንድንጠራ ይፈልጋል። በቅርቡ፣ ነብዩ ጆሴፍ ስሚዝ ከተወሰኑ የቤተክርስቲያኗ አባሎች ጋር ብቻ በመሆን፣ “ይህች ቤተክርስቲያን ሰሜንና ደቡብ አሜሪካን ትሞላለች—ዓለምን ትሞላለች” ብሎ በተነበየበት በከርትላንድ ኦሃዮ ነበርኩኝ።” 7 ጌታ የዚህን ዘመን ስራ “አሰደናቂ እና ድንቅ ስራ” ሲል ገልጾታል 8 ፡፡ ጌታ “ሁሉንም … የምድር ወገኖች እንዲባረኩ” ስለሚያስችለው “በኋለኛው ቀን ስለሚፈፀመው[ ] ቃል ኪዳን” ተናገረ። 9

የዚህ ጉባኤ ቃላት በ55 ቋንቋዎች በቀጥታ እየተተረጎመ ነው። በመጨረሻም፣ እነዚህ ቃላት ከ220 በሚበልጡ አገራት እና ግዛቶች ውስጥ በሚገኙ በ97 ቋንቋዎች ይሰማሉ እንዲሁም ይነበባሉ።

ምስል
ዳግሞ ምፅዓት

አዳኙ በግርማ እና በክብር ሲመለስ፣ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን አባላት ከሁሉም አገራት፣ ከሁሉም ህዝቦች፣ ከሁሉም ዘሮቸ፣ ከሁሉም ቋንቋዎች እና ከሁሉም የአለም ባህሎች መካከል የወጡ ይሆናሉ።

እያደገ የመጣው የቤተክርስቲያኗ ተፅዕኖ

የተመለሰው የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስያን ተፅዕኖ የቤተክርስቲያን አባል ለሆኑት ብቻ አይደለም። በዘመናችን ውስጥ ባሉት ሰማያዊ መገለጦች ምክንያት፣ ወደ ምድር በተመለሰው ቅዱስ መጽሐፍ እና በመንፈስ ቅዱስ ኃይለኛ ስጦታ ምክንያት በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ያለው አለማመን ዓለምን ሲያጨልም እኛ የኮረብታ ላይ የሚያንፀባርቅ ብርሃን እንሆናለን። ምንም እንኳን ብዙዎች በአዳኙ ላይ ያላቸውን እምነት ዓለም እንዲሸፍነው ሊፈቅዱ የሚችሉ ቢሆኑም፣ እኛ “ከስፍራችን አንወጣም።” 10 የእኛ አባል ያልሆኑ ክርስቲያኖች ስለክርስቶስ ያለንን ሚና እና ትክክለኛ ምስክርነታችንን ይቀበላሉ። በጥርጣሬ የተመለከቱን እነዚያ ክርስቲያኖችም እንኳን አንድ ቀን እንደጓደኞች ይቀበሉናል። በእነዚህ በሚመጡት ቀናት በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንጠራለን።

ትክክለኛውን የቤተክርስቲያኗን ስም ወደፊት ለማስጓዝ ለምታደርጉት መልካም ጥረታችሁ እናመሰግናለን። ከሶስት ዓመት በፊት በተካሄደው ጉባኤ ላይ ፕሬዚዳንት ኔልሰን “የአዳኙን ቤተክርስቲያን ትክክለኛ ስም ለመጠቀም የምንሰጠው ጠንቃቃ ትኩረት … ወደተጨማሪ እምነት እና ታላቅ መንፈሳዊ ሀይልን ወደመቀበል እንደሚመራ” ቃል ገብተውልናል። 11

በዓለም ዙሪያ ያሉ ታማኝ ደቀመዛሙርት ይህን ቃል ኪዳን ተገንዝበዋል። 12

ከምስራቃዊ ዩናይትድ ስቴትስ የመጣው ወንድም ላውሪ አሆላ፣ የቤተክርቲያኗን ሙሉ ስም ማካፈል አንዳንድ ጊዜ የማይመች ሆኖ እንዳገኘው አመነ። ሆኖም በነብዩ ምክር ምክንያት መጠቀሙን ቀጥሏል። በአንድ አጋጣሚ አንድን ጓደኛውን በአንድ የሌላ እምነት ቤተክርስቲያን እየጎበኘው ነበር። ንግግሩ በእርሱ አንደበት አነሆ፦

“አንድ ጓደኛ፣ ‘ሞርሞን ነህን?’ ሲል ጠየቀ።

“‘አዎ፣ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን አባል ነኝ፣ ’ አልኩኝ። እያንዳንዱ ጥያቄዎች ‘የሞርሞን ቤተክርቲያን …. ያምናልን?’ ብለው የሚጀምሩ የተለያዩ ጥያቄዎችን ይጠይቀኝ ጀመር እናም በእያንዳንዱ ጊዜ ‘በተመለሰው የክርስቶስ ቤተክርስቲያን … እናምናለን’ በሚል ሐረግ መልሴን ጀመርኩኝ።

“‘ሞርሞን’ የሚለውን መጠሪያ እንደማልቀበል ሲገነዘብ፣ በቀጥታ ‘ሞርሞን አይደለህምን?’ ብሎ ጠየቀኝ።

“ከዛ ሞርሞን ማን እንደነበር ያውቅ እንደሆነ ጠየቅኩት—አያውቀውም። ሞርሞን ነብይ እንደነበር … እናም [በእሱ] መጠራቴ [ለእኔ] ክብር እንደሆነ ነገርኩት።

“‘ነገር ግን’ ብዬ ቀጠልኩኝ፣ ‘ሞርሞን ለሃጢየቶቼ አልሞተም። ሞርሞን … በጌተሰማኒ ውስጥ አልተሰቃየም ወይም በመስቀል ላይ [ለእኔ] አልሞተም። … ኢየሱስ ክርስቶስ የኔ አምላክ እና አዳኜ ነው። … እናም በእርሱ ስም ነው እኔ መታወቅ የምፈልገው። …’

“…ከትንሽ የዝምታ ሰከንዶች በኋላ [ጓደኛው በመደነቅ]፣ ‘ስለዚህ ክርስቲያን ነህ ማለት ነዋ!’” አለ። 13

ምስል
ፕሬዚዳንት ኔልሰን በአጠቃላይ ጉባኤ ላይ

የፕሬዚዳንት ኔልሰንን ቃላት ታስታውሳላችሁ? “የጌታን ቤተክርስቲያን ትክክለኛ ስም ዳግም ለመመለስ የምንችለውን ያህል ጥረት ካደረግን፣ የዚህ ቤተክርስቲያን ባለቤት የሆነው እርሱም ሀይሉን እና በረከቶቹን በኋለኛ ቀን ቅዱሳን ራሶች ላይ ከዚህ በፊት አይተነው በማናውቀው መንገድ እንደሚያፈስ ቃል እገባላችኋለሁ።” 14

ጌታ ሁል ጊዜ መንገዱን ይከፍታል።

ጌታ ሁል ጊዜ ቃልኪዳኖቹን ይጠብቃል። ስራውን ስንሰራ መንገዱን ለእኛ ሁሌም ይከፍትልናል።

ChurchofJesusChrist.org እና ChurchofJesusChrist.com የሚሉትን የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያዎች ለመግዛት ለዓመታት ተስፋ አድርገን ነበረ። ሁለቱም ለሽያጭ የቀረቡ አልነበሩም። ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማስታወቂያውን ሊናገሩ ሲሉ አካባቢ ሁለቱም በድንገት ተገኙ። ተዓምር ነበር። 15

ጌታ ከቤተክርቲያኗ ጋር ለረጅም ጊዜ የተሳሰሩ ስሞችን የመከለስ ጥረታችንን አጉልቷል።

በእምነት ወደ ፊት በመጓዝ የሞርሞን ታበርናክል መዘምራን ስም ወደ የታበርናክል መዘምራን በቤተመቅደስ አደባባይ በሚል ተቀይሯል። በየወሩ ከ21 ሚሊዮን በላይ ጉብኝቶችን የሚቀበለው LDS.org የሚለው ድረ ገፅ ወደ ChurchofJesusChrist.org ተቀይሯል 16 ። LDS የቢዝነስ ኮሌጅ የሚለው ወደ ኢንዛይን ኮሌጅ ተቀይሯል። Mormon.org የሚለው ድረ ገጽ ChurchofJesusChrist.org ወደሚለው ተዛውሯል። “Mormon” ወይም “LDS” የሚሉ ስያሜዎችን የያዙ ከአንድ ሺህ በላይ የሚሆኑ ምርቶች ተቀይረዋል። ታማኝ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የድረ ገፃቸውን፣ የፖድካስት እና የትዊተር አካውንቶቻቸውን አስተካክለዋል።

ምስል
አዲስ የቤተክርስቲያን ምልክት

ኢየሱስ ክርስቶስን ያማከለ አዲስ ምልክት ተቀብለናል።

“በምልክቱ ማዕከልም በቶርቫልድሰን የተሰራ የእብነ በረድ ሐውልት ክርስተስ.ምስል ይገኛል። ከሞት የተነሳው፣ ህያው ጌታ ወደ እርሱ የሚመጡትን ሁሉ ለማቀፍ ክንዶቹን ከፍቶ ያሳያል።

“በምሳሌያዊ ሁኔታ ኢየሱስ ክርስቶስ በቅስት ስር በመቆም ትንሳኤ ያደረገው አዳኝ ከመቃብሩ ሲወጣ [ያስታውሰናል]።” 17

ምስል
የቤተክርስቲያኗ ስም በቋንቋዎች
ምስል
የቤተክርስቲያኗ ስም በተጨማሪ ቋንቋዎች

የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን ከ50 በላይ በሚሆኑ ቋንቋዎች ፊደሎች ተስተካክለዋል። አዲስ የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያ ስሞች በዓለም ዙሪያ ተገኝተዋል።

ለሌሎች እርዳታ አድናቆት ማሳየት።

በትክክለኛው ስያሜያችን ለመጠራት ያለንን ፍላጎት ያከበሩ እጅግ ብዙ መልካም እና ቸር ሰዎችን እናደንቃለን። አንድ የካቶሊክ ካርዲናል “የኋለኛው ቀን ቅዱሳን” ብሎ መጥራቱን የሚጠቅስበትን አንድ ፅሁፍ በቅርቡ አነበብኩኝ። 18 ከአንድ ወር በፊት በምስራቃዊ ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ አንድ የክርስቲያን ቤተክርስቲያን መሪ ጋር ስጎበኝ፣ በመጀመሪያው የእሱ አገላለፅ ውስጥ ቤተክርስቲያኗን በመላ ስያሜያችን ጠራ ከዚያም ከአንድ በላይ “የኢየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን” ብሎ አከለበት።

በስማችን ላይ ስድስት ቃላትን መጨመር ለሚዲያ እንደማይመች እንገነዘባለን፣ ነገር ግን ፕሬዚዳንት ኔልሰን አስቀድመው እንደተነበዩት “ሃላፊነት የሚሰማው ሚዲያ ለጥያቄያችን የሚሰጠው ምላሽ ሩህሩህ ይሆናል”። 19 ለባህላዊ፣ የአትሌቲክስ፣ የፖለቲካ ወይም የማህበራዊ ድርጅቶች የምንፈልገውን ስም በመጠቀም ተመሳሳይ አስተሳሰብ ስላበረከታችሁ እናመሰግናለን።

የተልዕኮአችንን ቆራጥነት ለማዘናጋት ወይም ለማሳነስ ተስፋ የሚያደርጉ የተወሰኑ ይኖራሉ፣ “ሞርሞኖች” ብለው መጥራታቸውንም ይቀጥላሉ። 200 ከሚጠጋ ዓመታት በፊት እንጠራበት በነበረው ስያሜ የመጠራት ፍላጎታችንን እንዲያከብሩ ፍትሃዊውን ሚዲያ በድጋሚ በአክብሮት እንጠይቃለን።

የኋለኛው ቀን ቅዱሳን ድፍረት

የቤተክርስቲያኗን ስያሜ በድፍረት ያወጁ በሺዎች የሚቆጠሩ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን አሉ። የራሳችንን ድርሻ ስናደርግ፣ ሌሎቹ ይከተላሉ። ይህን የታሂቲ ታሪክ እወደዋለው።

የአስር ዓመቷ ኢሪውራ ጄን የፕሬዚዳንት ኔልሰንን ምክር ለመከተል ወሰነች።

“በትምህርት ቤት ክፍሏ ውስጥ ቅዳሜ እና እሁድ ስለሚያደርጉት ነገር ተወያዩ … እናም ኢሪውራ ስለቤተክርስቲያን ተናገረች።

“አስተማሪዋ ቫይት ፒፋኦ እንዲህ መለሰች ‘ኦ፣ እና ሞርሞን ነሻ?’

“ኢሪውራ በድፍረት፣ ‘አይ፣ … የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የእየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን አባል ነኝ!’ ስትል ተናገረች።

“አስተማሪዋም እንዲህ መለሰች፣ ‘አዎ፣ … ሞርሞን ነሽ።’

“ኢሪውራ አጥብቃ፣ ‘አይደለም ቲቸር የኋለኛው ቀን ቅዱሳን የእየሱስ ክርስቶስ ቤተክርስቲያን አባል ነኝ!’

“ወ/ሪት ፒፋኦ በኢሪውራ ፅኑ እምነት ተደንቃ ነበር እናም ለምን ያን ያህል የቤተክርስቲያኗን ረጅም ስም ለመጠቀም እንደፈለገች ተገረመች። [ስለቤተክርስቲያኗ የበለጠ ለማወቅ ወሰነች።]

“[በኋላ እህት] ቫይት ፒፋኦ እንደተጠመቀች፤ ኢሪውራ የፕሬዚዳንት ኔልሰንን ምክር ስለሰማች [ምስጋናዋን ገልጻለች]።” 20

ምስል
በተማሪዋ ምክንያት ስለቤተክርስቲያኗ ያወቀችው እህት

“የቤተክርስቲያኗ ስም ለድርድር የሚቀርብ አይደለም።” በእምነት ወደፊት እንሂድ። በሕያው ነብዩ በተገለፀው መሰረት የጌታን ምክር በፍቃደኝነት ስንከተል በተለይም ከቀድሞ አስተሳሰባችን በተቃራኒው የሚሄድ ከሆነ፣ ትህትናን እና መስዋዕትነትን የሚጠይቅ ቢሆንም፣ ጌታ በተጨማሪ መንፈሳዊ ኃይል ይባርከናል እንዲሁም እንዲረዱን እና ከጎናችን እንዲቆሙ መላዕክቶቹን ይልካል 21 ። የጌታን ማጽደቅ እና ማረጋገጫ እንቀበላለን።

ሰማያዊ ሃይል በተወደደው ነብያችን በፕሬዚዳንት ረስል ኤም. ኔልሰን ላይ እንደሆነ የአይን ምስክር ነኝ። የእሱ ብቸኛ ፍላጎት ጌታን ማስደሰት እና የሰማይ አባት ልጆችን መባረክ ነው። ከተቀደሰ የግል ልምድ በመነሳት፣ እሱ የጌታ ነብይ እንደሆነ እመሰክራለሁ። እርሱ የእግዚአብሔር ነቢይ ነው።

“ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን እና የህያው እግዚአብሔር ልጅ መሆኑን እመሰክራለሁ። በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።

ማስታወሻዎች

  1. 3 ኔፊ 27፥7–9ትምህርት እና ቃልኪዳኖች 115፥4ን ይመልከቱ።

  2. ራስል ኤም. ኔልሰን በ “ፕሬዚዳንት ኔልሰን ስለቤተክርስቲያኗ ስም ተወያዩ፣” የዜና ክፍል፣ ነሃሴ 16፣ 2018 (እ.አ.አ)፣ newsroom.ChurchofJesusChrist.org።

  3. ፕሬዚዳንት ኔልሰን ስለቤተክርስቲያኗ ስም ተወያዩ“፣” የዜና ክፍል፣ ነሃሴ 21፣ 2018 (እ.አ.አ)፣ newsroom.ChurchofJesusChrist.org.

  4. ራስል ኤም.ኔልሰን፣ “የቤተክርስቲያኗ ትክክለኛ መጠሪያ፣” ሊያሆና፣ህዳር 2018 (እ.አ.አ)፣ 87።

  5. ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “The Temple and Your Spiritual Foundation፣” ሊያሆና፣ህዳር 2021 (እ.አ.አ)፣ 94።

  6. ትምህርት እና ቃልኪዳኖች 54፣32

  7. Teachings of Presidents of the Church: Joseph Smith (እ.አ.አ)(2007), 137.

  8. 2 ኔፊ 27፥26

  9. 1 ኔፊ 15፥18

  10. ትምህርት እና ቃልኪዳኖች 101፥17

  11. ራስል ኤም. ኔልሰን ፣ “አርአያ የኋለኛው ቀን ቅዱሳን መሆን፣” ሊያሆና፣ህዳር 2018( (እ.አ.አ)፣ 114፡፡

  12. ሔንሪ ቢ. አይሪንግ፣ “Thus Shall My Church Be Called፣” ሊያሆና፣ ጥቅምት 2021 (እ.አ.አ)፣ 6–9 ይመልከቱ።

  13. ላውሪ አሆላ፣ “Using the Full Name of the Church Was Awkward but Worth It፣”(በኤሌክትሮኒክ መልክ ብቻ የቀረበ ጽሁፍ) ሊያሆና፣፣ ሚያዚያ 2020 (እ.አ.አ)፣ ChurchofJesusChrist.org።

  14. ራስል ኤም.ኔልሰንን፣ “የቤተክርስቲያኒቷ ትክክለኛ መጠሪያ፣” 89።

  15. ከ2006(እ.አ.አ) ጀምሮ የቤተክርስቲያኗ አእምሯዊ ንብረት ጥበቃ ቢሮ ChurchofJesusChrist.org የሚለውን የቤተክርስቲያኗን የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያ ስም ሲከታተል ነበር እናም አይገኝም ነበር። ፕሬዚዳንት ኔልሰን ማስታወቂያውን በተናገሩ በተመሳሳይ ጊዜ ለገበያ መቅረቡ አስደናቂ ነበር፤ እናም ቤተክርስቲያኗ የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያ ስሙን በጣም መጠነኛ በሆነ ዋጋ ገዛች።

    በተመሳሳይ መልኩ፣ ከ2011 (እ.አ.አ) ጀምሮ ChurchofJesusChrist.com የሚለው የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያ ስም ስላለበት ሁኔታ እና ስለመኖሩ ቤተክርስቲያኗ ክትትል ጀምራ ነበር። በሚያስገርም ሁኔት እሱም በነሃሴ 2018 (እ.አ.አ) ተገኘ እና ተገዛ።

  16. በጥቅምት 2018 (እ.አ.አ) አጠቃላይ ጉባኤ ፕሬዚዳንት ኔልሰን እንዲህ አሉ፦

    “ወንድሞች እና እህቶች፣ የቤተክርስቲያኗ ትክክለኛ ስም በዳግም መመለስን የሚሞግቱ ብዙ አለማዊ ክርክሮች አሉ። የምንኖርበት ኣለም የዲጂታል አለም በመሆኑ እንዲሁም ስለጌታ ቤተክርስቲያን የምንፈልገውን መረጃ ጨምሮ የምንፈልጋቸውን መረጃዎች ወዲያውኑ እንድናገኝ የሚረዱን የመረጃ ማፈላለጊያ ሶፍትዌሮች በማደጋቸው ምክንያት ተቺዎች የቤተክርስቲያኗን ስም ማስተካከል ጥበባዊ አይደለም ይላሉ።

    “… የጌታን ቤተክርስቲያን ትክክለኛ ስም በዳግም ለመመለስ የምንችለውን ያህል ጥረት ካደረግን፣ የእርሱ ቤተክርስቲያን የሆነው እርሱም ሀይሉን እና በረከቶቹን በኋለኛ ቀን ቅዱሳን ራሶች ላይ ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ መንገድ እንደሚያፈስ ቃል እገባላችኋለሁ”(”The Correct Name of the Church፣” 88, 89)።

    LDS.org ወደ ChurchofJesusChrist.org ከተዛወረ ጀምሮ የኢንተርኔት የግዛት ጣቢያ ስም ስልጣን (ደረጃ የመስጠት ችሎታ እና ሃይል) በፊት ከነበረው ጠንክሯል። ለምሳሌ አንድ ሰው “church” ብሎ በሚፈልግበት ጊዜ የChurchofJesusChrist.org መነሻ ገጽ አሁን እና ላለፈው አንድ ዓመት በጉግል ፍለጋ ውጤት በአሜሪካ አንደኛ ነበር፤ ይህም ከዚህ በፊት ሊጠበቅ አይችልም ነበር።

  17. ራስል ኤም. ኔልሰን፣ “Opening the Heavens for Help፣” ሊያሆና፣ ግንቦት 2020 (እ.አ.አ)፣70።

  18. ታድ ዋልች፣ “‘If we can’t get along, it’s downright sinful’: The partnership between Catholics and Latter-day Saints,” Deseret News፣ ሐምሌ 1፣ 2021 (እ.አ.አ) deseret.com።

  19. ራስል ኤም.ኔልሰን፣ “የቤተክርስቲያኒቷ ትክክለኛ መጠሪያ፣” 89።

  20. The Correct Name of the Church: A Tahitian Story፣“Pacific Newsroom፣ መስከረም 15፣ 2019 (እ.አ.አ)፣ news-nz.ChurchofJesusChrist.org.

  21. ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 84፥88ይመልከቱ።

አትም