አጠቃላይ ጉባኤ
ሁለቱ ታላላቅ ትዕዛዛትን ማያያዝ
የአጠቃላይ ባለስልጣኖች፣ የክልል ሰባዎች እና አጠቃላይ መሪዎች ድጋፍ


ሁለቱ ታላላቅ ትዕዛዛትን ማያያዝ

ኢየሱስ ክርስቶስን ለመከተል ያለን ብቃት፣ የመጀመሪያይቱን እና ሁለትኛዪቱን ትእዛዛት በተመጣጠነ መንገድ እና ለሁለቱም እኩል ቅናዓት በማሣየት ለመኖር ባለን ጥንካሬ እና ሀይል ላይ የተመሠረተ ነው።

መግቢያ

ባለቤቴ ሌሳ እና እኔ የሚሠጠንን የሥራ ምደባ ለማከናወን በአለም ዙሪያ ስንጓዝ፣ በትልቅም ሆነ በትንሽ ስብሰባዎች ላይ ከእናንተ ጋር የመገናኘታችንን እድል እንወደዋለን። ለጌታ ስራ ያላችሁ ጥብቅ አምነት ከፍ ያደርገናል እንዲሁም የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል ምስክር በመሆን ይቆማል። ከእያንዳንዱ ጉዞ ስንመለስም የተቀበልነውን ያህል መልሰን ሠጥተን ይሆን በማለት እናስባለን።

ምስል
የሬንቦ ድልድይ።
ምስል
ሲንግ ማ ድልድይ።
ምስል
ታወር ድልድይ።

በጉዟችን ላይ፣ ነገሮችን ለመጎብኘት በጣም ትንሽ ጊዜ ነው ያለን። ይህም ቢሆን፣ በሚቻልበት ጊዜ አንድ በምወደው ነገር ላይ ጥቄት ጊዜ አሳልፋለሁ። የህንጻ አሰራርን እና ንድፍን እወዳለሁ እንዲሁም ድልድዮች ያስደንቁኛል። የተንጠለጠሉ ድልድዮችን በጣም ያስደንቁኛል። የቶኪዮ ሬንቦ ድልድይም ሆነ፣ የሆንግ ኮንግ ጻንግ ማ ድልድይ ወይም፣ የለንደን የማማ ድልድይ፣ ወይም ያየኋቸው ሌሎች ፣ በእነዚህ ውስብስብ ግንባታዎች ውስጥ ለመገንባት የተጠቀሙት የምህንድስና ጥበብ በጣም ያስደንቀኛል። ድልድዮች ያለድልድይ መሄድ ወደማንችልባቸው ቦታዎች ይወስዱናል። (ከመቀጠሌ በፊት፣ ይህ መልእክት የተዘጋጀው በቦልቲሞር ከደረሰው አሰቃቂ አደጋ በፊት ነበር። ለጠፉት ህይወት እናዝናለን እናም በዚህ ለተነኩት ቤተሰቦች መፅናናት እንመኛለን።)

አስደናቂ የተንጠለጠለ ድልድይ

በቅርብ ጊዜ፣ የጉባኤ ምድብ ወደካሊፎርኒያ ወሰደኝ፣ በዚያም እንደ የዓለም ምህንድስና ድንቅ በሚቀጥረው ታዋቂው የጎልደን ጌት ድልድይ ለመሻገር ቻልኩኝ። ይህ አስደናቂ መዋቅር ወብ ቅርፅን፣ ጠቃሚ አላማን፣ እና የምህንድስና ጥበብን አጣምሮ ይዟል። ይህም በጥጉ ላይ ትልቅ ማማ ያለው፣ በጣም ትልቅ በሆኑ ምሶሶዎች የሚደገፍ ተንጠላጣይ ድልድይ ነው። ከውቅያኖስ በላይ የወጡት ግዙፍ፣ ግርማ ሞገስ የተላበሱ መንትያ ማማዎች የተገነቡት የመጀመሪያዎቹ ነገሮች ናቸው። አብረውም የሚያንጠለጥለውን ዋናው የብረት ገመድ እና መንገዱን የሚያቅፈውን ቀጥ ያለውን የብረት ገመድ ክብደት ይሸከማሉ። የዚህ ማማ ድንቅ የማጠናከር ብቃትና ሀይል ይህ ድልድይ እንዲሰራ ያደረገው የምህንድስና ጥበብ ሚስጥር ነው።

ምስል
ጎልደን ጌት ድልድይ በእድሳት ላይ።

የጎልደን ጌት ድልድይ ዲስትሪክት

ድልድዩ በመጀመሪያ ሲገነባ የተነሱት ፎቶዎች ስለዚህ የምህንድስና መርሆ ይመሰክራሉ። ሁለቱ ተዛማጅ ማማዎች፣ በመደጋገፍ ተያይዘው፣ ለእያንዳንዱ የድልድዩ ክፍል ድጋፍ ይሰጣሉ።

ምስል
ጎልደን ጌት ድልድይ በእድሳት ላይ።

የጌቲ ምስሎች/አንደርዉድ አርካይቭስ

ሁለቱ ማማዎች በቦታቸው ሆነው ሲጠናቀቁ እና ምሶሶዎቹ በአለቱ ንጣፍ መሠረት ላይ ሲተከሉ፣ የወብት እና የጥንካሬ ምሳሌዎች ይሆናሉ።

ምስል
የጎልደን ጌት ድልድይ።

ዛሬ በጠንካራ መሠረት ላይ የተገነቡ ወደ ላይ የወጡ ማማዎች ያሉትን ይህን አስገራሚ ድልድይ በወንጌል አስተያየት እንድትመለከቱ እጋብዛችኋለሁ።

አሁን ቅዱስ ቀን ብለን በምናውቀው በኢየሱስ ክርስቶሥ የአገልገሎት ማብቂያ ቀናት፣ ህግ አዋቂ የሆነ ፈሪሳዊ ለመመለስ ከባድ እንደሆነ የሚያውቀውን ጥያቄ እንዲህ ብሎ ጠየቀው፦ “መምህር ሆይ፥ ከሕግ ማናቸይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት?” “ሊፈትነው” እና ሀቀኝነት በጎደለው አላማ ህጋዊ የሆነ መልስ የፈለገው ህግ አዋቂው ልባዊ፣ የተቀደሰ፣ መለኮታዊ መልስ ተቀበለ።

“ኢየሱስም እንዲህ አለው። ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ።

“ታላቂቱና ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት።” ወደ ድልድይ ምሳሌ በማመልከት፣ ይህም የመጀመሪያው ማማ ነው!

“ሁለተኛውም እንደ መጀመሪያቱ ነች፤ ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ።” ይህም ሁለተኛው ማማ ነው!

“በእነዚህ በሁለቱ ትእዛዛት ሕጉም ሁሉ ነቢያትም ተሰቅለዋል።” የሚቀሩት የድልድይ ክፍሎች።

በኢየሱስ ክርስቶስ መልሶች የተገለጹትን እና የተጠቀሱትን እነዚህን ታላቅ ትእዛዛት እንመርምር። ይህን ስናደርግ፣ ማማዎቹ ወደ ሰማይ የሚዘረጋውን የአስገራሚው ድልድይ እይታ በአዕምሮአችሁ ተመልከቱ።

ጌታን መውደድ

የመጀመሪያው ጌታን በሙሉ ልባችሁ፣ ነፍሳችሁ፣ እና አዕምሮአችሁ መውደድ ነው።

በመልሱ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ በብሉይ ኪዳን ቅዱስ ትምህርት ውስጥ ያለውን ህግ አጠቃለለ። ጌታን መውደድ የሚጀመረው ዋነኛ ተፈጥሯችሁ በሆነው በልባችሁ ነው። ጌታ የተቀደሰ አካላችሁ በሆነው በፍፁም ነፍሣሳችሁ፣ እና በመጨረሻም በፍፁም አዕምሮአችሁ ይኸውም በእውቀታችሁ እና በማሰብ ችሎታችሁ እንድትወዱ ይጠይቃችኋል። ለእግዚአብሔር ያለ ፍቅር የተገደበ ወይም መጨረሻ ያለው አይደለም። መጨረሻ የሌለው እና ዘለአለማዊ ነው።

ለእኔ፣ የመጀመሪያውን ትእዛዝ መተግበር አንዳንዴ ረቂቅ እንዲሁም የከበደ ሊሆን ይችላል። ምስጋና በሚገባው መልክም፣ ኢየሱስ የተናገራቸውን ቃላት ሳስብ፣ ይህ ትእዛዝ ይበልጥ ለመረዳት የሚቻል ይሆናል፦ “ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ።” ይህን ማድረግ እችላለሁ። የሰማይ አባትን እና ኢየሱስ ክርስቶስን ለመውደድ እችላለሁ፣ ይህም ወደ ጸሎት፣ ቅዱሳት መጻህፍትን ወደማጥናት፣ እና በቤተመቅደስ ወደ ማምለክ ይመራል። አብን እና ወልድን የምንወደው አስራቶችን በመክፈል፣ ቅዱስ ሠንበትን በማክበር፣ በስነ-ምግባር የታነፀ እና ንጹህ ህይወት በመኖር፣ እና ታዛዥ በመሆን ነው።

ጌታን መውደድ የሚመዘነው በትናንሽ እና በየቀኑ በሚከናወኑ ስራዎች፣ ቃል ኪዳኖችን ለመጠበቅ እና ለማጠናከር በሚደረጉ ጥረቶች ነው፦ ለወጣቶች ጌታን መውደድ ማለት፣ ማህበራዊ ሚድያን ለማፍረስ ሳይሆን ለመገንባት መጠቀም፤ መመዘኛዎች በሚፈተኑበት ጊዜ ከፓርቲ፣ ከፊልም ወይም እየተከናወኑ ካሉ ድርጊቶችመውጣት፤ ቅዱስ ለሆኑ ነገሮች ጥልቅ አክብሮትን ማሳየት ነው።

ይህን ምሳሌ አስቡ። እኔ እና ቫንስ አንድን ደባባ በር ስንኳኳ የጾም እሁድ ነበር። እኛ እና ሌሎች በቡድን ውስጥ አባል የሆንን ዲያቆናት፣ በደጁ ውስጥ ለመስማት በሚያስችል ወፍራም የጀርመን ዘዬ ሞቅ ባለ ድምፅ “እባካችሁ ግቡ” የሚሉትን ቃላት ሲጮሁ ለመስማት ጠብቀን ነበር። እህት ሚውለር በአጥቢያው ውስጥ ካሉት በርካታ ስደተኛ መበለቶች አንዷ ነበሩ። ዓይነ ስውር ስለነበሩ በሩን በቀላሉ መመለስ አይችሉም ነበር። ደብዛዛ ብርሃን ወዳለው ቤት ውስጥ ስንገባ፣ በደግነት ጥያቄዎች ተቀበሉን፦ ስምህ ማን ነው? እንዴት ነህ? ጌታን ትወዳለህ? የጾም በኩራትን ልንቀበል እንደመጣን ነገርናቸው። ገና በለጋ ዕድሜያችን፣ የድህነት ሁኔታቸው ግልፅ ሆኖ ይታየን ነበር፣ እና በእምነት የተሞላ ምላሻቸውም በጣም ልብ የሚነካ ነበር፦ “ዛሬ ጠዋት ላይ አንድ ሳንቲም ጠረጴዛ ላይ አስቀምጫለሁ። የጾም በኩራቴን ለመስጠት ስለቻልኩኝ በጣም አመስጋኝ ነኝ። በፖስታው ውስጥ ልታስቀምጠው እና የጾም በኩራት ደረሴን ልትሞላልኝ ትችላለህን?” ከቤታቸው በሄድን ቁጥር ፍቅራቸው እምነታችንን ከፍ ያደርገው ነበር።

ንጉስ ቢንያም፣ ፊተኛይቱን ታላቅ ትእዛዝ ለሚከተሉት አስደናቂ ሀይል እንደሚኖራቸው ቃል ገብቷል። “እናም በተጨማሪ፣ የእግዚአብሔርን ትዕዛዛት የሚጠብቁትን የተባረከና አስደሳቹን ሁኔታ እንድትገነዘቡ እፈልጋለሁ። … እነርሱ በሁሉም ነገሮች የተባረኩ ናቸው፣ እናም እስከ መጨረሻው በታማኝነት ከዘለቁ፣ ለዘለአለም በማያልቀው ደስታ ከእግዚአብሔር ጋር ይኖሩ ዘንድ፣ መንግስተ ሰማይ ትቀበላቸዋለች።”

ጌታን መውደድ ወደ ዘለአለማዊ ደስታ ይመራል።

ባልንጀራህን እንደ ነፍሥህ ውደድ

ከዚያም ኢየሱስ እንዲህ አለ፣ “ሁለተኛይቱም ይህችን ትመስላለች እርስዋም ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ የምትለው ናት።” ይህም የድልድዩ ሁለተኛው ማማ ነው።

እዚህ ላይ፣ ኢየሱስ፣ ጌታን ለመውደድ ወደ ሰማይ የምንመለከተውን፣ ሠዎችን ለመውደድ ምድራዊ ወደ ውጭ ከምንመለከተው ድልድይ ጋር ያገናኛል። አንዱ ከሌላው ጋር የሚደጋገፍ ነው። ባልንጀራን ችላ የምንል ከሆንን ለጌታ ያለን ፍቅር ሙሉ አይሆንም። ይህ በውጪ የሚታይ ፍቅር፣ ጾታን፣ የህብረተሰብ መደብን፣ ዘርን፣ የጾታ ምርጫን፣ የገቢ መጠንን፣ እድሜን፣ ወይም ብሄረሠብን ከግምት ውስጥ ሳያስገባ፣ የእግዚአብሔር ልጆችን ሁሉ ያካትታል። “ሁሉም በእግዚአብሔር ዘንድ አንድ [ስለሆኑ] የተጎዱትን እና የተሰበሩትን፣ የተገለሉትን እንፈልጋቸዋለን ።” “ደካማውን [እንደግፋለን]፣ የዛሉትን እጆች [እናቀናለን]፣ እናም የሰለሉትን ጉልበቶች [እናጠናክራለን]።”

ይህን ምሳሌ አስቡበት፦ ወንድም ኤቭንስ መኪናውን እንዲያቆምና የማያውቀውን ቤተሰብ በር እንዲያንኳኳ የመንፈስ መነሣሣት ሲቀበል ተደንቆ ነበር። ከ10 በላይ ልጆች እናት የሆነችው መበለት በሩን ስትከፍት፣ የነበሩባቸው አስቸጋሪ ሁኔታዎች እና ታላቅ ፍላጎቶቻቸው ግልፅ ሆኑለት። የመጀመሪያውና ቀላሉ ቤቱን ቀለም መቀባት ነበር፣ ያም የብዙ አመታትን ስጋዊ እና መንፈሳዊ አገልግሎት አስከተለ።

በኋላም፣ ይህች አመስጋኝ እናት ከሰማይ ስለተላከው ጓደኛዋ እንዲህ ስትል ጻፈች፦ “ህይወትህን በሙሉ ከሁሉ ያነስነውን እኛን ስትረዳ ኖረሀል። አንተ እና እርሱ ብቻ የምታውቋቸውን ሰዎች በገንዘብ እና በመንፈሳዊ ላደረግከው መልካም ነገር አድናቆቱን ሲገልጽ ጌታ የሚግርህን ነገሮች ብሰማ እንዴት ደስ ይለኛል። በብዙ መንገዶች ስለባረከን እናመሰግንሀለን፣ … ስለላክልን ሚስዮናውያንም እንዲሁ። … ጌታ አንተን በልዩ መርጦህ ይሆን ወይስ የሰማኸው አንተ ብቻ ትሆን ይሆን ስል በብዛት አስባለሁ።”

ባልንጀራን እንደራስ መውደድ የክርስቶስ አይነት የደግነት እና የአገልግሎት ተግባራትን ያካትታል። የያዛችሁትን ቂም ለመርሳት፣ ጠላቶቻችሁን ይቅር ለማለት፣ ለባልጀሮቻችሁ መልካም አቀባበል በማድረግ ለማገልገል፣ እንዲሁም አዛውንቶችን ለመርዳት ፈቃደኛ ለመሆን ትችላላችሁን? እያንዳንዳችሁ ለባልጀራችሁ የመውደድ ማማችሁን ስትገነቡ መነሳሻ ታገኛላችሁ።

ፕሬዚዳንት ራስል ኤም. ኔልሰን እንዲህ ሲሉ አስተምረዋል፦ “ለሌሎች እርዳታ መስጠት፣ እንዲሁም ለእኛ እንደምናስበው ወይም ከዚያም በላይ በጥንቃቄ ሌሎችን መንከባከብ የእኛ ደስታ ነው። በተለይም አመቺ ሣይሆን ሲቀር ወይም ከምቾት ቦታችን ሲያስወጣን … ። ሁለተኛይቱን ታላቅ ትዕዛዝ መኖር እውነተኛ የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀመዝሙር ለመሆን ቁልፍ ነው።”

እርስ በርስ መደጋገፍ

ኢየሱስ በተጨማሪ እንዳስተማረው፣ “በእነዚህ በሁለቱ ትእዛዛት ሕጉም ሁሉ ነቢያትም ተሰቅለዋል።” ይህም በጣም የሚያስተምር ነው። ጌታን በመውደድ እና እርስ በርስ በመዋደድ መካከል አስፈላጊ መደጋገፍ አለ። የጎልደን ጌት ድልድይ የተገነባበትን ዓላማ እንዲያከናውን፣ ሁለቱም ማማዎች በእኩል ሀይል ደረጃ ጠንካራ መሆን እና የተንጠለጠለውን የብረት ገመድ፣ የሚነዳበትን መንገድ፣ እንዲሁም ድልድዩን ተሻግረው የሚሄዱትን መኪናዎች ክብደት በእኩል መሸከም አለባቸው። በሁለቱ ወገን እኩል የሆነው የምህንድስና ንድፍ ባይኖር ኖሮ፣ ድልድዩ ጥንካሬውን ወደማጣት እና ተሰብሮ ወደመውደቅ ያመራ ነበር። ማንኛውም ተንጠልጣይ ድልድይ የተገነባበትን ዓላማ ለማከናወን፣ ማማዎቹ በሙሉ ስምምነት አብረው መስራት አለባቸው። በተመሣሣይ መንገድ፣ ኢየሱስ ክርስቶስን ለመከተል ያለን ብቃት፣ የመጀመሪያይቱን እና ሁለትኛዪቱን ትእዛዛት በተመጣጠነ መንገድ እና ለሁለቱም እኩል ቅናዓት በማሣየት ለመኖር ባለን ጥንካሬ እና ሀይል ላይ የተመሠረተ ነው።

ምስል
የጎልደን ጌት ድልድይ።

ሆኖም፣ በአለም ላይ እየጨመረ የመጣው ብጥብጥ አንዳንዴ ይህን ለማየት ወይም ለማስታወስ እንደማንችል ይጠቁማል። አንዳንዶች ትእዛዛትን በመጠበቅ ላይ እጅግ በማተኮር አነስ ያለ ፅድቅ እንዳላቸው ለሚያስቧቸው ሰዎች አነስተኛ መቻቻልን ያሳያሉ። አንዳንዶች፣ ህይወታቸውን ከቃል ኪዳኑ ውጪ ለመኖር ወይም ከማንኛውም የሀይማኖት ተሣትፎ ውጪ ለማድረግ የሚመርጡትን ለመውደድ ይቸገራሉ።

በሌላ በኩል፣ በእግዚአብሔር ተጠያቂ መሆናቸውን ሳይቀበሉ ሁሉንም በመውደድ አስፈላጊነት ላይ የሚያተኩሩም አሉ። አንዳንዶች ፍጹም እውነት ወይም ትክክል እና ስህተት የሚባሉ ሃሳቦች ስለመኖራቸው አይቀበሉም፣ እንዲሁም ከእኛ የሚጠበቀው የሌሎችን ምርጫዎች ሙሉ በሙሉ መታገስ እና መቀበል ብቻ ነው ይላሉ። እነዚህ ሁለቱም ያልተመጣጠኑ ነገሮች መንፈሳዊ ድልድያችሁ ወደአንድ ጎን እንዲንጋደድ ወይም እንዲወድቅ ሊያደርጉ ይችላሉ።

ፕሬዚዳንት ዳልን ኤች. ኦክስ የሚከተለውን በተናገሩ ጊዜ ይህን ገልጸዋል፦ “የኢየሱስ የደጉ ሳምራዊ ምሳሌ ሁሉም ባልንጀራችን እንደሆኑ ስለሚስተምር፣ ሁሉንም እንድንወድ ታዝዘናል። ነገር ግን ሁለተኛይቱን ትዕዛዝ የመጠበቅ ከፍተኛ ፍላጎታችን እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ የሚለውን የመጀመሪያውን እንድንረሳ ማድረግ የለበትም፡፡”

መደምደሚያ

ስለዚህ ለሁላችንም የሚቀርበው ጥያቄ ይህ ነው፦ እግዚአብሔርን መውደድ እና ባልንጀሮቻችንን መውደድ የሆኑትን ረጃጅም የድልድይ ማማዎችን በመገንባት የራሳችንን የእምነት እና የቅንዓት ድልድይ እንዴት ለመገንባት እንችላለን? እንግዲህ፣ እንጀምር። የመጀመሪያ ጥረታችን፣ እንገነባለን ብለን ተስፋ የምናደርገውን ድልድይ በናፕኪን ጀርባ ላይ እንደተጻፈ እቅድ ወይም የመጀመሪያ ደረጃ ንድፍ ሊመስል ይችላል። ይህም የጌታን ወንጌል ይበልጥ ለመረዳት ሊደረስባቸው በሚችሉ ጥቂት ግቦች ላይ መስራትን ወይም ሌሎች ላይ መፍረድን ለመቀነስ መሀላ መግባትን ሊያካትት ይችላል። ማንም ለመጀመር በጣም ወጣት ወይም በጣም ያረጀ አይሆንም።

ምስል
የድልድይ ቅርጽ ንድፍ

ከጊዜ በኋላ፣ በጸሎት እና በታሰበበት እቅድ፣ ጥሬ ሀሳቦች ይዳብራሉ። አዲስ ድርጊቶች ልማድ ይሆናሉ። የመጀመሪያው አላማ የተጣራ ንድፍ ይሆናል። ለሰማይ አባት እና ለአንድያ ልጁ እንዲሁም አብረናቸው ለምንሰራው ለምንጫወተው፣ ወይም ለምንኖረው ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን መለኮታዊ በሆኑ ልቦች እና አዕምሮዎች የግል መንፈሳዊ ድልድያችንን እንገነባለን።

ከፊታችን ባሉት ቀናት፣ ወደ ላይ ከፍ ያሉ ማማዎች ያሏቸው ድንቅ በሆኑ ተንጠልጣይ ድልድዮች ላይ ስትሄዱ ወይም ፎቶ ስትመለከቱ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የተገለጹትን ሁለቱን ታላቅ ትእዛዛት አስታውሱ። የጌታ ትምህርት ያነሳሳን። ልባችን እና አዕምሮአችን ጌታን ለመውደድ ወደ ላይ ከፍ ይበሉ እንዲሁም ባልንጀራችንን ለመውደድም ወደ ውጪ ይዙሩ።

ይህም በምመስክርባቸው በኢየሱስ ክርስቶስ እና በኃጢያት ክፍያው ያለንን እምነት ያጠናክሩ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም፣ አሜን።

ማስታወሻዎች

  1. በአዲስ ኪዳን ውስጥ፣ [ህግ አዋቂ የሚለው ቃል] ከጸሀፊ ጋር ተመሳሳይ ነው፣ ይህም የተጻፉትን የአምስቱ መፅሀፍ ህግጋት እና ደግሞም ‘የሽማግሌዎችን ባህል’ (ማቴዎስ 22፥35ማርቆስ 12፥28ሉቃስ 10፥25) የሚያካትት የህግ ባለሙያ ተማሪ ወይም አስተማሪ ነው” (Bible Dictionary, “Lawyer”)።

  2. በጥንት ጊዜ የአይሁድ ሊቃውንት በኦሪት ውስጥ 613 ትእዛዛትን ዘርዝረው ነበር እናም የአንዱ አንጻራዊ አስፈላጊነት ከሌላው ጋር በንቃት ተከራክረዋል። ምናልባት ጠበቃው የኢየሱስን መልስ እርሱን ለመቃወም ሊጠቀምበት አስቦ ሊሆን ይችላል። ከሁሉ የሚበልጠው አንዱ ትእዛዝ እንደሆነ ከተናገረ፣ ኢየሱስ የሕጉን ሌላ ገጽታ ችላ በማለት ለመወንጀል መክፈቻ ሊፈቅድ ይችላል። ነገር ግን የአዳኙ ምላሽ እርሱን ለማጥመድ የመጡትን ዛሬ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለምናደርጋቸው ነገሮች ሁሉ መሰረት እንደሆነ በመሠረታዊ መግለጫ ጸጥ አሰኛቸው።

  3. ማቴዎስ 22፥36–40

  4. ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 88፥15 ይመልከቱ።

  5. ዮሀንስ 14፥15

  6. በታሪኩ ውስጥ ያሉ ሁለቱም ስሞች ምስጢራዊ ለማድረግ ተቀይረዋል።

  7. ሞዛያ 2፥41።

  8. ማቴዎስ 22፥39.

  9. 2 ኔፊ 26፥33

  10. ትምህርት እና ቃል ኪዳኖች 81፥5

  11. ስሞች ምስጢራዊ ለማድረግ ተቀይረዋል።

  12. ራሰል ኤም. ኔልሰን፣ “ሁለተኛው ታላቅ ትእዛዝ፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2019 (እ.አ.አ)፣ 100።

  13. ማቴዎስ 22፥40

  14. ዳለን ኤች. ኦክስ፣ “ሁለቱ ታላቅ ትእዛዛት፣” ሊያሆና፣ ህዳር 2019 (እ.አ.አ)፣ 73–74።

አትም